ፋሲለደስ

ፋሲለደስ

Monday, December 26, 2011

አዲስ አበባ እንዴት እና ወዴት?


አዲስ አበባ እያደገች ነው፡፡ በዚህ ነዋሪዎቿም፣ መሪዎቿም፣ ቀያሾቿም፣ አልሚዎቿም ይስማማሉ፡፡ እንዴት እና ወዴት የሚለው ግን ሁሉንም የሚያሟግት ጉዳይ ነው፡፡ ከተወሰነ ግዜ በፊት በአዲስ አበባ የከተማ ልማት እድገት ዙሪያ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ለመስራት አቅጄ ከላይ የጠቀስኳቸውን አራት አካላት አነጋግሬ ነበር፡፡ እነዚህ አካላት የሚከተሉትን አስተያየቶች ሰጥተውኛል፡፡

ከባለሙያዎች አንጻር በርካታ ልምድ ያላቸውን አራት የሚሆኑ አርክቴክቶች ያናገርኩ ሲሆን ከሞላ ጎደል ተመሳሳይ እይታ ነው ያላቸው፡፡ የአዲስ አበባን በፍጥነት እያደገች መሆን ሁሉም አርክቴክቶች ይስማሙበታል ነገር ግን ትክክለኛውን የእድገት ጎዳና ስለመከተሏ ጥያቄ አላቸው፡፡

እንደባለሙያዎቹ እይታ በከተማዋ የሚሰሩ ህንፃዎች የጥራት ደረጃ አጠያያቂ ነው፡፡ አንድ ህንፃ ማሟላት ከሚገባው መሰረታዊ ጉዳዮች አንጻር ቢታይ እንኳ የጣሪያ ከፍታ ማነስ፣ የአደጋ ግዜ መውጫ አለመኖር፣ በቂ የመኪና ማቆሚያ አለመኖር የመሳሰሉት ችግሮች ጎልተው ይታያሉ፡፡ ባለሙያዎቹ እንደሚሉት አንድ ህንፃ በአንድ ቦታ ሲሰራ የአካባቢውን አቀማመጥ፣ ታሪክ፣ ባህል እና ነዋሪ ከግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ ዲዛይኑ መሰራት ሲገባው ባብዛኛው በአዲስ አበባ የሚሰሩ ህንፃዎች ከሌላ ቦታ መጥተው የበቀሉ ባዕድ ነገሮች ነው የሚመስሉት፡፡ የሃገሪቱን እና አካባቢውን እሴት ባካተተ መልኩ እየተሰሩ አይደለም፡፡ ለዚህ ዋነኛው ችግር ደግሞ አብዛኞዎቹ ባለሙያዎች የህንጻ ዲዛይን ሲሰሩ ወሳኞቹ እነሱ ሳይሆኑ ደንበኞቻቸው ስለሆኑ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ የመስተዋት ህንጻ መሰራት በሌለበት ቦታ ላይ የመስታዋት ህንፃ፣ የመስተዋት ህንጻ መሰራት ባለበት ቦታ ላይ ደግሞ የብሎኬት ወይንም የሸክላ አሊያም በሌላ ጥሬ እቃ የተሰራ ህንጻ የምናገኘው፡፡ 

በአንድ አካባቢ የተሰሩ ህንጻዎችን ስንመለከት ደግሞ እርስ በእርስ የመናበብ ችግር ያለባቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በአንድ መስመር ላይ የሚሰሩ ህንጻዎችን ብናይ እንኳ አንዱ ህንጻ ወደ መንገድ ገባ ብሎ ሲሰራ ሌላው ከመንገድ ወጣ ብሎ፣ አንዱ በብሎኬት፣ አንዱ በመስተዋት፣ አንዱ በሸክላ፣ ሌላው በሴራሚክ በመሳሰሉት በተዘበራረቀ መልክ የተሰሩ ናቸው፡፡ ጎን ለጎን በቆሙ ህንጻዎች መካከል የአንዱ ህንጻ ከፍታ እጅግ ረዝሞ የሌላው ደግሞ እጅግ አጥሮ ያልተመጣጠነ የከፍታ ልዩነት የሚስተዋልባቸው ህንጻዎችንም በከተማችን በብዛት እንደሚስተዋሉ አርክቴክቶቹ ታዝበዋል፡፡ የጎንዮሽ ስፋታቸውም አንዱ እጅግ ቀጥኖ እና አንዱ ሰፍቶ ይስተዋላል፡፡ ከቀለም አንጻር ደግሞ ሁሉም የመሰለውን ቀለም የሚቀባበት ልምድ እንዳለ ይገልጻሉ፡፡ እንደ አርክቴክቶቹ እምነት በአንድ አካባቢ የሚሰሩ ህንጻዎች የአካባቢ ልማት ፕላንን ተከትለው መሰራት የሚገባቸው ሲሆን ይህን ፕላን ተከትለው የማይሰሩ ከሆነ ግን አሁን እንደሚስተዋለው የተዘበራረቀ እይታን ይፈጥራሉ፡፡

ህንጻ መሰራት ባለበት ቦታ ቪላ ቤት፣ ቪላ መሰራት በሚገባው ቦታ ህንጻ፣ መናፈሻ ሊሆን የሚገባው የገበያ ማዕከል ወይንም የህንፃ ቦታ የሆኑ አካባቢዎች በከተማዋ የሚደጋገሙ ናቸው፡፡ በተለይ የህዝብ መናፈሻ ወይንም አረንጓዴ ቦታ የአንድ ከተማ ሳንባ ተደርጎ የሚቆጠር ሲሆን በአዲስ አበባ የህዝብ መናፈሻ ወይንም አረንጓዴ ቦታ ችላ ተብሏል፡፡  

ባለሙያዎቹ አዲስ አበባ ምን ትመስላለች ለሚለው ጥያቄ ይህን ትመስላለች ለማለት አስቸጋሪ ነው ይላሉ፡፡ እንደባለሙያዎቹ ገለጻ አዲስ አበባ አምስት ስድስት አይነት መልክ ያላት ሲሆን ይህን አይነት የተዘበራረቀ መልክ ያለው ከተማ በሌሎች ሃገሮች አይስተዋልም፡፡ 

የከተማዋ እድገት የሚበረታታ ቢሆንም እያደገች ያለችበት መንገድ ግን ሊጤን ይገባል ይላሉ፡፡ እንደእነሱ ገለጻ በአሁኑ ወቅት ህንጻ እየተሰራ ያለው በአብዛኛው በእንጨት ተሰርተው የነበሩ ያረጁ እና የደከሙ ቤቶች እየፈረሱ ሲሆን ይህ የሚያስከፍለው ዋጋ አነስተኛ ነው ነገር ግን የህንጻ አሰራራችን እና የአከባቢ ልማት እድገቱ በዚህ መልክ ከቀጠለ ይህን ለማስተካከል ወደፊት ህንጻዎችን ማፍረስ ሊጠበቅብን ነው ይህ ደግሞ እጅግ ውድ ዋጋ ያስከፍለናል፡፡

ከዚህ በፊት የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በብሄራዊው የቴሌቪዥን ጣቢያ ሲናገሩ እንደሰማሁት ከተማዋ ብዙ አይነት መልክ እንዳላት እና የመንግስታቸው ጥረትም ቢያንስ ሁለት መልክ ያላት ከተማ ለማድረግ መጣር እንደሆነ ነው፡፡ ይህን የእርሳቸውን አስተያየት ከሰማሁ በፊትም ሆነ ከግዜያት በሗላ በከተማዋ የተለያዩ ለውጦች የተደረጉ ሲሆን በተለይ የመንገድ እና የኮንዶሚኒየም ስራ ትኩረት ተሰጥቶት ሲሰራ ቆይቷል፡፡ ከዚህ ባለፈ ደግሞ በተለያዩ የከተማዋ ዝቅተኛ መንደሮች እንዲፈርሱ እና ለባለሃብት እንዲሰጡ ወይንም ሌላ ልማት እንዲከናወንባቸው እየተደረገ ነው፡፡ ያነጋገርኳቸው የከተማ ልማት ባለስልጣናት ይህ እንቅስቃሴ መንግስት ለከተማዋ እድገት ትኩረት ሰጥቶ እሰራ መሆኑን ያሳያል ይላሉ፡፡  

በህንጻ ዲዛይን እና የአካባቢ ልማት እድገት ዙሪያ ባለሙያዎች ለሚያነሱት ጥያቄ ግን ለራሳቸው ለባለሙያዎቹ ነጻነት ለመስጠት እና ፈጠራን ለማበረታታት ስንል ያደረግነው ነው የሚሉት፡፡ ያም ሆኖ የከተማዋ እድገት የተዘበራረቀ ነው ለሚለው ለዘብ ያለ አቋም ያላቸው ሲሆን እንደ ባለስልጣናቱ እምነት ከተማዋ በትክክለኛ የእድገት ጎዳና ላይ ትገኛለች፡፡ በከተማዋ የሚስተዋሉ አንድ አንድ ችግሮች የባለሙያዎች እና ባለሃብቶች ችግሮች ናቸው ይላሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል አንድ ባለሃብት ህንጻ ሲያሰራ አረንጓዴ ቦታ መተው ሲገባው ያለክፍት ቦታ ሙሉ ለሙሉ ህንጻ የሚያሰራ ከሆነ ችግሩ የባለሃብቱ ነው ይላሉ፡፡

አብዛኞቹ ባለሃብቶች ህንጻ ለመስራት ቦታ በሊዝ መግዛት የሚጠበቅባቸው ሲሆን የሊዝ ዋጋ ውድ መሆን በሚሰሩት ህንጻ የጥራት ደረጃ ላይ የራሱ አሉታዊ ተፅእኖ እንዳለው ገልጸዋል፡፡ በከፍተኛ ዋጋ በሊዝ መሬት ከገዙ የገዙትን መሬት ሙሉ ለሙሉ “በአግባቡ” ሊጠቀሙበት እንደሚፈልጉ እና መንግስት ለአረንጓዴም ሆነ ለመኪና ማቆሚያ በሚል ከሚሸጥላቸው ቦታ ላይ ከሊዝ ነጻ የሚሰጣቸው እንደሌለ ይገልጻሉ፡፡ ስለዚህም አርንጓዴ ቦታ መተው ውድ ዋጋ ያወጡለትን ቦታ እንደማባከን እንደሚቆጥሩት ነው የገለጹት፡፡

የባለሙያዎች የመወሰን አቅም ማነስ ከባለሃብቶች በሚመጣ ከፍተኛ ተፅዕኖ እንዳልሆነም አስተባብለዋል፡፡ በእርግጥ ውጭ ያዩትን ህንጻ ዲዛይን አይነት በአዲስ አበባ የመስራት ፍላጎት እንዳላቸው ቢገልጹም የበለጠ ትኩረት የሚሰጡት ግን የጥሬ እቃ በቅርብ እና በርካሽ መገኝት፣ የህንጻው በፍጥነት ማለቅ እና ቶሎ አገልግሎት ላይ መዋል የመሳሰሉት ጉዳዮች እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ 

አንድ አንድ ባለሃብቶች የሚያሰሩትን ህንጻ ኮንትራክት ደረጃውን ላልጠበቀ ተቋራጭ መስጠት በህንጻዎች ዲዛይን እና ግንባታ ወቅት ለሚያጋጥሙ መሰረታዊ ችግሮች እንደምክንያት ጠቅሰዋል፡፡ የባለሃብቶቹ እርስ በእርስ አለመናበብም ሌላው ችግር መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ 

የከተማዋ ነዋሪዎች የአዲስ አበባን እድገት በበጎ አይን ቢመለከቱትም እድገቱ መሰረታዊ ችግሮቻቸውን ፍትሃዊ በሆነ መልኩ በሚፈታ መልክ አለመሆኑ ይበልጥ ያሳስባቸዋል፡፡ በመንግስት በኩል ነዋሪዎችን የቤት እጥረት ለመፍታት ከፍተኛ ጥረት እተደረገ መሆኑ ቢነገርም ከፍተኛ መኖሪያ ቤት እጥረት እንዳለ ይናገራሉ፡፡

ከዚህ ባለፈ ደግሞ በአሁኑ ወቅት ለልማት በሚል በርካታ መንደሮች እየፈረሱ ሲሆን እነዚህ መንደሮች ሲፈርሱ የነዋሪዎቹን ችግር ትኩረት ሰጥቶ ሊፈታ በሚችል መልኩ ቢሰራ መልካም ነው ይላሉ፡፡ ነዋሪዎቹ ከቤታቸው እንዲፈናቀሉ ሲደረግ በቂ ዋስትና አለማግኘት እንዲሁም የሚሰጣቸውን ምትክ ኮንዶሚኒየም ለመግዛት አቅም ማነስ፣ ሲኖሩበት ከነበረው ቦታ አንጻር ከሚያከናውኑት ማህበራዊ እና ምጣኔሃብታዊ እንቅስቃሴ ጋር እጅግ የማይጣጣም ቦታ መመደብ የመሳሰሉ ችግሮች ጎልተው እንደሚታዩም በምሬት ጭምር ገልፀውልኛል፡፡ 

ነዋሪዎቹ እና ባለሙያዎቹ በይበልጥ ትኩረት የሰጡበት ጉዳይ የከተማ ልማት እድገት መንገድ እና ህንጻ ግንባታ ላይ ብቻ ትኩረት ያደረገ ሳይሆን የነዋሪውን እና ሰራተኛውን ዘርፈብዙ እንቅስቃሴ በሚያሳልጥ መልኩ ሰው ተኮር የከተማ ልማት እድገት ቢሆን መልካም መሆኑን ነው፡፡

Thursday, December 15, 2011

የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኝነት እና ተግባራዊው እውነታ


በመሰረቱ ስፖርት ሲባል ባህላዊውንም ዘመናዊውንም ጨምሮ አብዛኛዎቻችን ልንዘረዝራቸው የምንችላቸው የአካል እንቅስቃሴ እና ጥልቅ እሳቤን የሚጠይቁ ሁሉንም አይነት ጨዋታዎች ያጠቃልላል፡፡ ከመገናኛ ብዙሃን ፍላጎት አንጻር ስፖርት ከፍተኛውን ድርሻ ይዞ የቆየ የመዝናኛ ፕሮግራም ሲሆን አሁን አሁን ደግሞ ከመዝናኛነትም ያለፈ ጉዳይን እየሆነ ይገኛል፡፡


ስፖርት እንደ አንድ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ እና ምጣኔ-ሃብታዊ ጉዳይ ራሱን የቻለ ሰፊ ርዕሰ ጉዳይ እየሆነ የመጣ ሲሆን ሊሰጠው የሚገባው ግምትም ያን ያህል እየከበደ መጥቷል፡፡ በመሆኑም እነዚህን ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ እና ምጣኔ-ሃብታዊ ጉዳዮች ብቻ የሚተነትኑ የተለያዩ መገናኛ ብዙሃን እንዳሉ ሁሉ ስፖርታዊ ጉዳዮችን ብቻ የሚተነትኑ ጋዜጦች፣ ሬድዮኖች፣ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች፣ ድረ-ገጾች እና ሌሎች መገናኛ ብዙሃን በርካታ ናቸው፡፡


በኢትዮጵያም ስፖርታዊ ጉዳይን ብቻ የሚተነትኑ ጋዜጦች እና ድረ-ገጾች ያሉ ሲሆን በሬድዮ እና ቴሌቪዥን ጣቢያዎችም ለስፖርታዊ ጉዳዮች ከሌሎቹ ርዕሰ-ጉዳዮች አንጻር ተመጣጣኝ ባይሆንም ፍትሃዊ የአየር ሰዓት ተመድቧል ማለት ይቻላል፡፡


እዚህ ላይ ግን ከበርካታ በዙሪያየ ካሉ ሰዎች የተለያዩ አስተያየቶችን አደምጣለሁ፡፡ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ዋናው ጉዳያቸው ስፖርት ይመስል ወሪያቸው ሁሉ ስፖርት ሆነ የሚሉ አሉ፡፡ በእውነትም ፖለቲካዊ፣ማህበራዊ እና ምጣኔ-ሃብታዊ ጉዳዮችን እና ስፖርትን በአንድ ላይ ጨፍልቆ ለሚያቀርብ የሬድዮ ወይንም የቴሌቪዥን ጣቢያ ስፖርት ይህን ያህል የአየር ሰዓት ማግኘቱ የቀደመውን አስተያየት ሊያስነሳ ይችላል፡፡ ነገርግን ስፖርት በራሱ ካለው ዘርፈ ብዙ ጉዳይ አንፃር እንዲያውም ከላይ ከጠቀስኳቸው ሶስቱ ዋና ጉዳዮች ጋር መጨፍለቁ ተገቢዉን ትኩረት እንዳያገኝ አድርጎታል የሚል ሃሳብ ነው ያለኝ፡፡ እንደሌሎች ሃገራት ስፖርታዊ ጉዳዮችን ብቻ የሚያቀርቡ የሬድዮ እና የቴሌቪዥን ጣቢያዎች አለመኖራቸው ተጎጂ እንዳደረገን አምናለሁ፡፡


ነገር ግን በአሁኑ ወቅት በሃገር ቤት እየተተገበረ ያለው የስፖርት ጋዜጠኝነት ምን ያህል ሙያዊ እና ስነምግባራዊ ነው ለሚለው እኔም በርካታ አሉታዊ አስተያየቶች አሉኝ፡፡


በአብዛኛው ለሃገርቤት መገናኛ ብዙሃን ስፖርት ማለት የእግር ኳስ ጨዋታ ሆኗል ያውም የአውሮፓ ክለቦች የእግር ኳስ ጨዋታ፡፡ የእግር ኳስ ጨዋታ ካለው አዝናኝነት፣ ከተመልካቹ ብዛት እና ከሚያንቀሳቅሰው ከፍተኛ ገንዘብ አንጻር በጋዜጣ ላይ የሰፋውን ቦታ እና በሬድዮ እና ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ላይ ደግሞ የበዛውን የአየር ሰዓት ቢይዝ የጎላ ጥያቄ ላያስነሳ ይችላል፡፡ ሆኖም በእኔ ዳሰሳዊ ግምት በተለያየዩ የኤፍ ኤም እና የኤ ኤም ሬድዮ ጣቢያዎች ከሚቀርቡ የስፖርት ዝግጅቶች ብዙውን ግዜ ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ሁኔታ እና አንድ አንድ ግዜ ከዘጠና በመቶ በላይ  የእግር ኳስ ጉዳይ የሚተነተን ሲሆን ከዚህም የሚበዛው የአውሮፓ የእግር ኳስ ክለቦች ጨዋታ ጉዳይ ነው፡፡


ይህ የሆነበት ምክንያት በተለያዩ ጉዳዮች ተፅዕኖ ሊሆን ይችላል አንደኛ የእግር ኳስ በተለይም ደግሞ የአውሮፓ ክለቦች የእግር ኳስ ጨዋታ ከሌሎች ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች የተሻለ አዝናኝ ነው ተብሎ ስለሚገመት፤ ሁለተኛ በሃገር ውስጥ አብዛኛው የስፖርት አድናቂ ማህበረሰብ የእግር ኳስን በተለይም ደግሞ የአውሮፓ ክለቦች የእግር ኳስ ጨዋታን የበለጠ ይወዳል ተብሎ ስለሚገመት፣ ሦስተኛ ደግሞ በተለይ ከአውሮፓ ሃገራት መገናኛ ብዙሃን የሚለቀቁ እጅግ ብዛት ያላቸው እና የየክለቦቻቸውን ሁኔታ የሚተነትኑ መረጃዎች በተትረፈረፈ ሁኔታ ማግኘት መቻሉ የጋዜጠኞችን ትኩረት በመሳቡ ሊሆን ይችላል፡፡ በእነዚህም ሆነ በሌሎች ምክንያት የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን የአውሮፓ ክለቦችን የእግር ኳስ ጨዋታ ተንታኝ ሆኗል፡፡


የአውሮፓ ክለቦችን የእግር ኳስ ጨዋታ መተንተኑ ባይከፋም መገናኛ ብዙሃኑን በሚከታተለው ህብረተሰብ ዘንድ ሊፈጥር የሚችለው ተፅዕኖ ግን የተስተዋለ አሊያም በደንብ የተጠና አይመስለኝም፡፡ መረጃ ስለተገኘ ዝም ብሎ መተንተን ወይንም በመገናኛ ብዙሃን ማቅረብ ፋይዳው ምንድነው? እከሌ የሚባለው ቡድን አሸነፈ ወይንም ተሸነፈ መባሉ መልካም ሆኖ ሳለ የእከሌው ቡድን ተጫዋች ወይንም አሰልጣኝ እንዲህ አለ ተብሎ መቅረቡ ለኢትዮጵያን የመገናኛ ብዙሃን ተከታታዮች ጥቅሙ ምንድን ነው? እሱ እንዲህ ስላለ እና ምን ይሁን? ከዘገባው ጀርባ እነዚህን ጥያቄዎች መመለስ የሚቻል ከሆነ የዘገባው ፋይዳ (impact) ተለይቷል ማለት ነው ሆኖም የአብዛኞቹ ዘገባዎች ፋይዳ ምን ስለመሆኑ አቅራቢዎቹም ተከታታዮቹም ስለማወቃቸው እርግጠኛ አይደለሁም፡፡


በሚገርም ሁኔታ በአንድ አንድ የሃገር ውስጥ የስፖርት ጋዜጦች ደግሞ ሙሉ በሙሉ የአውሮፓ ክለቦች የእግር ኳስ ጨዋታ ጉዳዮች የሚቀርብባቸው ሲሆን የጋዜጣው ባለቤት አቋሙን በሚገልጽበት ኤድቶሪያል ላይ ግን ስለኢትዮጵያ ስፖርት አቋሙን ያቀርባል፡፡ በዘገቡት ጉዳይ ላይ አቋም መያዝ ሙያዊም ሞራላዊም ሲሆን ባልዘገቡት ጉዳይ ላይ አቋም መያዝ ግን አሁንም የዘገባ ፋይዳ የቱን ያህል እንደሆነ አለመረዳት ይመስለኛል፡፡


የሃገር ውስጥ ስፖርት የእግር ኳሱን ጨምሮ በአብዛኞቹ ስፖርታዊ ጉዳዮችን በሚያቀርቡ መገናኛ ብዙሃን ተገቢውን ትኩረት እያገኘ አይደለም፡፡ ይሄን ጉዳይ ቢያቀርቡ የተሻለ ለውጥ ማምጣት ስለመቻላቸውም እርግጠኞች አይደሉም፡፡ በአንድ ወቅት የደከመ ወይንም የተሻለ ውጤት ሲያስመዘግብ ሚናቸውን ባልለየ መልኩ ከመጯጯህ እና አስተያየት ከመስጠት ባለፈ በአዘቦት ግዜያት የሃገር ውስጥ ስፖርት በሃገር ውስጥ የስፖርት መገናኛ ብዙሃን ችላ እንደተባለ ነው፡፡


ከዘህ በተረፈ ግን የሩጫ፣ የቴንስ፣ የቦሊቦል፣ የጎልፍ፣ የገና ጨዋታ፣ የፈረስ ጉግስ፣ የገበጣ ጨዋታ እና የሌሎችም ስፖርታዊ ጨዋታዎች አድናቂዎች እነዚህን ዘገባዎች ከሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ለማግኘት ቢያንስ በወር አንዴ መጠበቅ አሊያም ራሳቸው ጨዋታዎቹ የሚካሄዱባቸው ቦታዎች በመሄድ ከቦታው መረጃ ማግኘት ግድ ሳይላቸው አልቀረም፡፡ 


የስፖርት እና የጥበብ (ART) ጋዜጠኝነት ከሌላው የጋዜጠኝነት ሙያ በተለየ እና በተሻለ መልኩ ለጋዜጠኛው የሚሰጠው ነጻነት እና መብት አለ እሱም ሙያው ጋዜጠኞቹ በሚዘግቡት ጉዳይ ላይ የግል አስተያየታቸውን እንዲሁም ትችታቸውን በማካተት ማቅረብ እንዲችሉ መፍቀዱ ነው፡፡ 


ይህ ጋዜጠኞቹ ሊያቀርቡት የሚችሉት የግል አስተያየት እና ትችት በጉዳዮቹ መሰረታዊ ሃሳብ እና እውነታ ላይ ተነስተው የተደራጀ እና ከስሜት የፀዳ ሃሳብ ከመስጠት ስሜታዊ አስተያየት እስከመስጠት እንዲችሉ ይፈቅዳል፡፡ ለምሳሌ አንድ ስፖርት ጋዜጠኛ አንድን የእግር ኳስ ተጫዋች “ይህ ተጫዋች የእግር ኳስ ከሚጫወት ቢያርስ ይሻል ነበር” እስከሚል ስሜታዊ አስተያየት ቢሰጥ በህግም በሥም ማጥፋት ሊያስጠይቀው አይችልም፡፡ 


ሆኖም የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ስፖርት የሚሉት እግር ኳስ ብቻ እንደሆነ እና እግር ኳሱም ያለው በአውሮፓ ክለቦች ዘንድ እንደሆነ እንቀበለው ብንልም እንኳ ይህንኑ የአውሮፓ ክለቦች እግር ኳስ የሚዘግቡበት መንገድም ግን የተሳሳተ ነው፡፡


የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያህል አንድ አንዶቹ የስፖርት ጋዜጠኞች “እኔ ብሆን ኖሮ ተጨዋቹ እንዲህ አደርግ ነበር፤ እኔ ብሆን ኖሮ አሰልጣኙ እንዲህ አይነቱን የጨዋታ አይነት እከተል ነበር” የመሳሰሉትን አስተያየት ሲሰጡ ይስተዋላል፡፡ ይሄ የጋዜጠኝነት ሚናን አለመለየት ነው፡፡ አሱ ጨዋታው እንዴት እንደተካሄደ፣ ምን ጠንካራና ደካማ ጎኖች እንደነበሩት፣ ምን ክስተት ተፈጥሮ እንደነበር መረጃ አጠናቅሮ እና የራሱን አስተያየት አክሎ ሊነግረን ሲገባ እርሱ ቢሆን ኖሮ ምን ሊያደርግ እንደሚችል ማውራቱ ማንነቱን ያለመለየቱ ችግር ይመስለኛል፡፡ 


ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ በስፖርት ዘገባዎች ላይ እውነታም አስተያየትም ያሆኑ ጉዳዮች ሲቀርቡ ይስተዋላሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል “እከሌ የተባለው አሰልጣኝ እንደዚህ አስቦ ነበር፣ እከሌ የተባለው ተጫዋች ፍላጎት እንዲህ ነበር” የመሳሰሉ ነገሮች በስፖርት ጋዜጦች ተፅፈው ማንበብ እና በሬድዮ እና ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ሲነገሩ ማዳመጥ አዲስ አይደለም፡፡ በዚህ ግዜ እኔ የጋዜጠኞቹን ሰብዓዊ ፍጡርነት እጠራጠራለሁ፡፡ አንድ አሰልጣኝ የተናገረውን ለማወቅ ጋዜጠኛ መሆን በቂ ሲሆን ይህ አሰልጣኝ ያሰበውን ለማወቅ ግን አንድም አሰልጣኙ ይህን አስቢያለሁ ብሎ መናገር አለበት አንድም ጋዜጠኛው ሰው የሚያሰበውን የሚያውቅ የተለየ ፍጡር መሆን አለበት፡፡ እርግጠኛ ሆኜ ለመናገር ግን የአውሮፓ መገናኛ ብዙሃን ጋዜጠኞች እንዲህ አይነት ዘገባ አያቀርቡም፡፡


ወገንተኛነት የሚስተዋልባቸው የጋዜጣ ሪፖርቶች፣ የሬድዮ የቀጥታ የስፖርት ስርጭቶች፣ እና የቴሌቪዥን ውይይቶችም የተለመዱ ሆነዋል፡፡ እነዚህን ዝግጅቶች የሚከታተሉ ሰዎች እከሌ የተባለው ጋዜጠኛ እከሌ ቡድን ደጋፊ ነው፣ እከሌ ደግሞ የእከሌን ቡድን ይጠላዋል ብለው በእርግጠኝነት መናገር እስኪችሉ ድረስ እነዚህ ወገንተኝነት የሚንጸባረቅባቸው ዘገባዎች አሉ፡፡


በሌላ በኩል ደግሞ ዋናው ርዕሰ ጉዳይ ተረስቶ ከጨዋታው ጋር የማይያያዙ ጉዳዮች በበለጠ ትኩረት ሲዘገቡ ይስተዋላል፡፡ እከሌ የተባለው አንድ የአውሮፓ ክለብ ተጫዋች የሴት ጓደኛ ስትደሰት እና ስትበሳጭ ምን እንደምታደርግ ጠቀመውም አልጠቀመውም ለኢትዮጵያዊ ስፖርት ተከታታይ ይቀርብለታል፡፡ አሁንም ጠቀመውም አልጠቀመው ስለተጫዋቹ አባት፣ እናት እና ሌሎች ዘመዶች ማንነት እና ምንነት እንዲያነብ ወይንም እንዲያዳምጥ ይደረጋል፡፡


እጅግ የሚከፋው ግን እንዲህ ከላይ የጠቀስኳቸውን ስህተቶች በሙሉ ባካተተ መልኩ የሚተገበረው የስፖርት ጋዜጠኝነት ትክክለኛው ስፖርት ጋዜጠኝነት እንደሆነ እየተወሰደ መምጣቱ ነው፡፡ አንድ ጉዳይ በተሳሳት መልኩ በተደጋጋሚ ሲተገበር እና ለየት ባለ መልኩ በተስተካከለው መንገድ ጉዳዩን የሚያቀርበው ሲጠፋ ያ የተሳሳተ መንገድ በዘልማድ ተቀባይነት ያገኘ መንገድ ሆኖ ይቀጥላል፡፡ ስፖርት ጋዜጠኝነትም በዚህ መልኩ እየነጎደ ሲሆን ይኄ ሙያውንም ባለሙያውንም ቀስ በቀስ መጉዳቱ አይቀርም፡፡ 


እንደኛ ጥቂት የመገናኛ ብዙሃን ብቻ ባሉበት ሃገር ከሌሎች ርዕሰ ጉዳዮች አንጻር እንደ ስፖርት እና ጥበብ በመሳሰሉ እና ከመንግስትም ሆነ ሌላ አካል ጋር ሊፈጥሩት የሚችሉት ግጭት አነስተኛ በሆኑ ርዕሰ ጉዳዮች ያሉ ዘገባዎች በዚህ መልኩ ሙያዊም ክህሎትም ሆነ ስነምግባራዊ ግዴታ የጎደላቸው ሆነው ሲገኙ የጋዜጠኞቹን እና መገናኛ ብዙሃኑን የብቃት ደረጃ ያጠያይቃል፡፡

Wednesday, November 30, 2011

ቅድመ ምርመራ፡ ከተቋማዊ አሰራር ወደ ውስጣዊ አሰራር

የቅድመ-ምርመራ (censorship) ፅንሰ ሃሳብ የመገናኛ ብዙሃን ፅንሰ ሃሳብ ሲጠነሰስ ጀምሮ የነበረ ቢሆንም ተቋማዊ በሆነ መልኩ እና በተደራጀ አቀራረብ ተግባራዊ የተደረገው ግን የቆዩ ከሚባሉ ከአራቱ የፕሬስ ቲየሪዎች ሶቬት-ኮሚኒስት የፕሬስ ቲየሪ (Soviet - Communist Theory of Press) የሚባለውን የፕሬስ ፍልስፍና ያራምዱ በነበሩ ሃገራት እና መንግስታት ነው፡፡

ይህን የፕሬስ ቲየሪ ከሞላ በጎደል ለመግለፅ ያህል መገናኛ ብዙሃን የመንግስት ወይንም የህዝብ ናቸው የሚል መነሻ ያለው ሲሆን በእነዚህ የመገናኛ ብዙሃን የሚተላለፉ ማንኛውም ጉዳዮች የመንግስቱን ወይንም የህዝቡን (የአብዮቱን) ፍላጎት እና ጥቅም ያማከሉ መሆን እንዳለባቸው እና ይህንንም ለማረጋገጥ ቅድመ-ምርመራ አስፈላጊ ስለሆነ በተቋም ደረጃ ተደራጅቶ ማንኛውም ስርጭት እና ህትመት ለህዝብ ከመድረሱ በፊት መመርመር ይኖርበታል የሚል አንድምታ አለው፡፡

ከ1966 እስከ 1983 በሰልጣን ላይ የቆየው የኢትዮጵያ መንግስት ይከተል የነበረው ፖለቲካዊ ፍልስፍና ሶሻሊዝም (ኮምዩኒዝም) ስለነበረ የመገናኛ ብዙሃን ቲየሪውም በዚህው መልኩ የተዋቀረ ነበር እናም የቅድመ-ምርመራ አሰራርን ተቋማዊ በሆነ አሰራር ተግባር ላይ አውሎት ቆይቷል፡፡ ይህ የመንግስትን አስተዳደር ሲመራ የቆየው አካል በ1983 ከወረደ በሗላ የፀደቀው አዲሱ ህገ-መንግስት ቅድመ-ምርመራን የተከለከለ ተግባር እንደሆነ ደንግጓል፡፡ ሆኖም የእኔ መከራከሪያ ነጥብ ቅድመ-ምርመራ አቀራረቡን ቀየረ እንጂ አሁንም አለ የሚል ነው፡፡

በህዝብ (በመንግስት) መገናኛ ብዙሃን ስላለው ቅድመ-ምርመራ ቀድሜ ላስረዳ፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ አንድ ጉዳይ ግልፅ ለማድረግ ያህል በኢትዮጵያ “የመንግስት” የሚባል መገናኛ ብዙሃን በህግ ደረጃ የለም፡፡ የኢትዮጵያ ሬድዮ እና ቴሌቪዥን ድርጅትም ሆነ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት በአዋጅ ደረጃ የህዝብ በሚል ነው የተቋቋሙት ሆኖም እንደ ማንኛውም ሃገር አብዛኛውን ግዜ የህዝብ ተቋማትን በአደራ የሚያስተዳድረው መንግስት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት መንግስት የህዝብን አደራ በመቀበል እነዚህን ተቋማት እያስተዳደረ የሚገኝ ሲሆን መንግስት የህዝብን አደራ እና ጥቅም ችላ በማለት ተቋማቱን በአሁኑ ወቅት ስልጣን ላይ ለሚገኘው የአስተዳደር አካል ጥቅም በሚያደላ መልኩ እየተጠቀማባቸው ስለሚገኝ ተቋማቱ ለመንግስት ያደሉ ናቸውና “የመንግስት” መገናኛ ብዙሃን የሚል ተቀትላ እንዲሰጣቸው ሆኗል፡፡

ይህ “የመንግስት” የሚለው ተቀጥላ ግን በራሱ የሚያስተላልፋቸው መልእክቶች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ከላይ ገለፅኩትን ሃሳብ የሚያጠናክር ሲሆን መንግስት የህዝብን አደራ መብላቱን እና ለህዝብ ጥቅም መዋል ያለበትን መገናኛ ብዙሃን ስልጣን ላይ ላለው አስተዳደር ጥቅም እየዋለ እንደሆነ ለመግለጽ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ተቃውሞን መግለጫ መንገድ ሲሆን በእነዚህ መገናኛ ብዙሃን የሚተላለፉ ጉዳዮች የህዝብን አቋም አያንጻባርቁም ፤የመንግስት ናቸው ስለዚህ አይወክሉንም የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ይመስላል፡፡

መንግስት በዚህ አይነት ሁኔታ የህዝብን መገናኛ ብዙሃን ሲያስተዳድር እና በስልጣን ላይ ያለውን አስተዳደር ጥቅም ለማስከበር ሲፈልግ በቅድሚያ መገናኛ ብዙሃኑን እንዲያስተዳድሩ የሚሾማቸው ሰዎች ህዝብ የሚያምንባቸውን እና በሙያቸውን ምስጉን የሆኑትን ሳይሆን ከገዢው ፓርቲ የተውጣጡ እና ከህዝብ ጥቅም ይልቅ ለድርጅታቸው ጥቅም ቅድሚያ የሚሰጡትን ነው፡፡ በዚህ ረገድ ከላይ የጠቀስኳቸውን ሁለቱንም ድርጅቶች የሚያስተዳድሩት እና የሚመሩት በህዝብ የተመረጡ ሳይሆን በገዢው ፓርቲ ወይንም አስተዳዳሪ የተመረጡ ሹመኞች መሆናቸው እርግጥ ነው፡፡ እነዚህ ሹመኞች ካላቸው የመወሰን ስልጣን አንጻር የድርጅቶቹ አሰራር ስልጣን ላይ ለሚገኘው አስተዳደር በሚያደላ መልኩ እንዲሆን ተፅዕኖ የማሳደር አቅማቸውም እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት በመገናኛ ብዙሃኑ የሚሰራጩ እና የሚተላለፉ ጉዳዮች በአሁኑ ወቅት እያስተዋልን እንዳለነው በመንግስት አስተዳደር ላይ ያለውን አካል በይፋ የሚደግፉ ካልሆነ ደግሞ ቢያንስ አስተዳደሩን የማይቃወሙ ወይንም የማይተቹ እንዲሆን ቅድመ-ምርመራ ይደረጋል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ በእነዚህ የመገናኛ ብዙሃን በሁለት መንገድ የሰራተኛ (ጋዜጠኛ) ቅጥር የሚካሄድ ሲሆን የመጀመሪያው በህጋዊው አሰራር መሰረት የድርጅቱን መስፈርት የሚያሟሉ ባለሙያዎች ተወዳድረው የተሻለ ውጤት ያስመዘገቡት የሚቀጠሩ ሲሆን ሁለተኛው የቅጥር መንገድ ደግሞ በልዩ ሁኔታ ግልጽ ባልሆነ መንገድ ከተለያዩ ክልሎች የተውጣጡ እና በመንግስት አስተዳደር ላይ ለሚገኘው አካል “እጅግ ታማኝ” የሆኑ በረኛ ጋዜጠኞች (gatekeepers) የሚቀጠሩበት አሰራር ነው፡፡ እነዚህ በረኞች ትምህርታቸውም ሆነ የስራ ልምዳቸው ከመገናኛ ብዙሃን ስራ ጋር ምንም ተያያዥነት የሌለው ሲሆን ዋናው ተፈላጊ ችሎታቸው በመንግስት አስተዳደር ላይ ለሚገኘው አካል ያላቸው ታማኝነት ነው፡፡

መንግስት ከህዝብ በአደራ የሚያስተዳድራቸው መገናኛ ብዙሃን ላይ የመወሰን የበላይነት ስላለው እነዚህን ታማኝ በረኞች በከፍተኛ የኤድቶሪያል ቦታዎች ያስቀመጣቸው ሲሆን ማንኛውም የሚሰራጭ እና የሚታተም ዜናም ሆነ ፕሮግራም ወይንም ሪፖርት በበረኞቹ በኩል ካልሆነ አያልፍም፡፡ በረኞቹ የመቁረጥ የመቀጠል ስልጣን ስላላቸው ማንኛውም ለህዝብ አገልጋይ ነኝ የሚል “የመንግስት” መገናኛ ብዙሃን ጋዜጠኛ የሰራው ዜና እና ፕሮግራም ወደደም ጠላ ለበረኞቹ መቀስ የተጋለጠ ነው፡፡ በአንድ አንድ ወቅቶች ደግሞ እንዲያውም በአሁኑ ጊዜ በአብዛኛው በረኞቹ የጋዜጠኛውን ሚና በመውሰድ ራሳቸው እየዘገቡ የሚገኝ ሲሆን ዘገባው በራስ ቅድመ-ምርመራ (self-censorship) የተቃኘ ነው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ በትክክለኛው መንገድ የተቀጠሩት የህዝብ መገናኛ ብዙሃን ጋዜጠኞችም ለራስ ቅድመ ምርመራ የተጋለጡ ናቸው፡፡ በተለያየ መንገድ ከበረኞቹ እና ከተሿሚ የመገናኛ ብዙሃኑ አመራር አካላት የሚደርስባቸውን አሉታዊ ተፅኖ ለመቋቋም ያላቸው ብቸኛው አማራጭ በራሳቸው ግዜ ዘገባቸው ላይ ቅድመ-ምርመራ ማድረግ ሲሆን ይህ ደግሞ የበለጠ አደገኛ ነው፡፡ ምክንያቱም ቅድመ-ምርመራ በባህሪው በመንግስት አስተዳደር ላይ ለሚገኘው አካል “ምቹ” ያልሆኑ ጉዳዮች ካሉ ያንን የሚቆጣጠር አካል የሚቆርጥ ሲሆን የራስ ቅድመ-ምርመራ ደግሞ አስፈላጊ መረጃዎችን በራስ ግዜ አለማካተት ነው፡፡

ከላይ በዘረዘርኳቸው ምክንያቶች “በመንግስት” መገናኛ ብዙሃን ቅድመ-ምርመራ አለ ልዩነቱ መልኩን መቀየሩ ነው እላለሁ፡፡ እንዴት መልኩን ቀየረ ለሚል ጥያቄ ደግሞ ቀድሞ የነበረው የቅድመ-ምርመራ አሰራር እራሱን በቻለ ውጫዊ አካል የሚሰራ እና ተቋማዊ አቀራረብ ያለው ሲሆን አሁን የተለወጠው ነገር ይህን የቅድመ-ምርመራ አሰራር መገናኛ ብዙሃኑ የውስጥ አሰራር አድርገው እንዲወስዱት እና በጋዜጠኞቹም አመለካከት ዘንድ እንዲሰርፅ መደረጉ ነው፡፡

የግል መገናኛ ብዙሃን ላይ ያለው ቅድመ-ምርመራ በተወሰነ መልኩ “በመንግስት” መገናኛ ብዙሃን ካለው የተለየ ነው፡፡ ቀለል ካለው ጉዳይ ብንነሳ ካለው ወቅታዊ ሁኔታ እንደምንረዳው የግል መገናኛ ብዙሃን ያላቸው የገንዘብ አቅም እና ሃብት (resource) ወሱንነት አንጻር በአስተዋወቂዎቻቸው እና ስፖንሰሮቻው ላይ መሰረት ያደረጉ ናቸው፡፡ ያም ሆኖ አብዛኞቹ የግል መገናኛ ብዙሃን ባለቤቶች እና መሪዎች ሲገልፁ እንደሚስተዋለው ያሉት አስተዋዋቂዎች እና ስፖንሰሮችም ያላቸው አቅም እና ብዛት ውስን ነው፡፡ እነዚህ ውስን አስተዋዋቂዎች እና ስፖንሰሮች ደግሞ አነሱም በዙ ያሉት የግል መገናኛ ብዙሃን ይዘዋቸዋል፡፡ በዚህ ላይ የአድቨርታይዝመንት ሳይንስ የእኛን በመሰለ ሃገር እጅግም ስላልሰረፀ የመገናኛ ብዙሃኑ እና አስተዋዋቂዎቹና የስፖንሰሮቹ ግንኙነት እንዲሁም መብት እና ግዴታ ግልፅ በሆነ አሰራር ሲመራ አይስተዋልም፡፡ እንዲያውም አስተዋዋቂዎች እና ስፖንሰሮች የሰፋውን የመወሰን ስልጣን ሲይዙ የሚታይባቸው አጋጣሚዎች አሉ፡፡ ስለሆነም መገናኛ ብዙሃኑ እነዚህን አስተዋዋቂዎች እና ስፖንሰሮችን ላለማስከፋት ይጠነቃቃሉ፡፡ ስለዚህ ማንኛውንም በአስተዋዋቂዎቻቸው እና ስፖንሰሮቻቸው ዙሪያ የሚያጠነጥኑ አሉታዊ ጉዳዮች ሳይዘግቡ ወይንም ተደባብሰው ሲታለፉ ይስተዋላል፡፡

ከዚህም ሌላ በተለይ ጋዜጦች በሌሎች ሃገራት እንዳለው አሰራር አብዛኛውን ገቢያቸውን የሚሰበስቡት ከአስተዋዋቂዎች እና ከስፖንሰሮች ሳይሆን ከወረቀት ሽያጭ ስለሆነ ጋዜጣቸውን ለመሸጥ ሲሉ አጀንዳ የመቅረፅ ትልቁን ሃላፊነታቸውን ለህዝቡ ወይንም ለአንባቢያቸው አሳልፈው ሲሰጡ ይስተዋላል፡፡  

ከዚህ የከፋው ግን እንደ “የመገናኛ ብዙሃን እና የመረጃ ነጻነት” እንዲሁም “የፀረ-ሽብርተኝነት” የመሳሰሉ አዋጆች በመውጣታቸው፣ በነፃነት መፃፍ የማይቻልበት ደረጃ ላይ መደረሱ፣ የጋዜጠኞች መታሰር እና መሰደድ እየተለመደ መምጣት የመሳሰሉት ጉዳዮች ደግሞ መገናኛ ብዙሃኑንም ጋዜጠኞቹንም ለራስ ቅድመ-ምርመራ እያጋለጣቸው መሆኑን በተለያየ መንገድ ገልፀዋል፡፡ ስለዚህ በግሉም መገናኛ ብዙሃን ውስጥ ቅድመ-ምርመራ ስራ ላይ እየዋለ ነው ማለት ነው፡፡

በዚህ ረገድ አሁንም ህዝቡ ማግኘት የሚገባውን ጠቃሚ መረጃ እያገኘ አይደለም ማለት ይቻላል፡፡ ከላይ በተዘረዘሩ የተለያዩ ምክንያቶች በግሉም ሆነ በመንግስት መገናኛ ብዙሃኑ ላይ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ቅድመ-ምርመራ እየተደረገ ስለሆነ በአንድ አንድ ዘገባዎች መረጃዎች እየተቆረጡ እና እተቀጠሉ ሲሆን በአንድ አንድ ዘገባዎች ደግሞ መረጃዎች ሳይካተቱ እየቀሩ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ህዝብ በማህበራዊ፣ ምጣኔ-ሃብታዊ እና ፖለቲካዊ ተሳትፎው ላይ የሚያደርገው እንቅስቃሴ በበቂ መረጃ ላይ ያልተመሰረተ አልያም በተሳሳተ መረጃ ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ስለሚያደርገው ወደ ተሳሳተ አቅጣጫ ይመራዋል፡፡

Tuesday, November 22, 2011

መፃፍ ጀምሬያለሁ

ከቅርብ ጊዜያት በፊት በአውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ላይ ሲጽፍ የቆየ አምደኛ “መፃፍ አቁሜያለሁ” በሚል ርዕስ አንድ ጠንከር ያለ አመክኖ ያለው የጽሁፍ ሃተታ አቅርቦ መጻፍ አቆመ፡፡ ይህንን ጽሁፍ ካንብበኩ በሗላ መፃፍ ብፈልግም መፃፍ ለመጀመር ብዙ ጊዜ ፈጀብኝ፡፡ ሆኖም መጻፍ ለመጀመር የቆሰቆሰኝ ዋናው ጉዳይ ይሄው ሲሆን አምደኛው መፃፍ ካቆመ በሓላ እንኳ ባለፉት ጊዜያት የሆኑት ጉዳዮች ደግሞ መፃፍ ለመጀመር ፈራ ተባ እያልኩ እንድቆይ አስገድደውኝ ሰንብተዋል፡፡ 

በእርግጥ አምደኛው መፃፍ ለማቆም የተገደደበት ዋናው ጉዳይ ምን ነበር ? 

አምደኛው በየሳምነቱ በሚፅፋቸው ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማሕበራዊ ጉዳዮችን በሚተነትኑ እና በሚተቹ ፅሁፎቹ ምክንያት ያልተደሰቱ ወገኖች እንዳይፅፍ እንቅፋት ሆኑበት፡፡ ዛቻ እና ማስፈራራት ሲያበዙበት እና በአንድም ሆነ በሌላ ምክንያት በህጋዊው መንገድ ሄዶ ሊያሸንፋቸው እንደማይችል ሲገምት እነዚህን ያልተደሰቱ ወገኖች ማስደሰት የሚቻልበት ብቸኛው አማራጭ መጻፍ በማቆም ብቻ እንደሆነ አመነ፡፡ እናም መፃፍ አቆመ፡፡ እሱ ሰላም ለማግኘት ሲል ወይንም ወህኒ ቤት እንዳይወረወር አሊያም ሕይወቱን ለማቆየት መጻፍ ማቆሙ ትክክል ነበር፡፡  

ነገር ግን ይህ አምደኛ መጻፍ በማቆሙም እርሱ እንደገለጸልን በሁለት ነገሮች ተጎዳ፤ አንድም በሕገ መንግስቱ ዋስትና ተሰቶት የነበረውን ሃሳቡን የመግለጽ ነጻነቱን ተገፈፈ፤ አንድም በመጻፍ ያገኝ የነበረው ገቢ ተቋረጠ፡፡ በእኔ እምነት የመጀመሪያው ጉዳት እጅግ የከፋ ነው ምክንያቱም በራሱ ሃገር እና በራሱ ጉዳይ ላይ የራሱ ሃገር ሰዎች ሲወስኑ እና ያሻቸውን ሲተገብሩ ዝም ብሎ መመልከትን የመሰለ የሚያስከፋ ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ መንግስትም ሆነ በተዋረድ ያሉ አካላት በሚያቀርቡት ሃሳብ ላይ ተጨማሪ ሃሳብ ማቅረብ ፣ ማስተካከያ ሃሳብ መሰንዘር፣ መተቸት እና መቃወም ሲቻል የቀረበው ሃሳብ እንደወረደ ተወስኖ እና ተተግብሮ ሊያደርስ የሚያስችለውን ጥቅምም ሆነ ጉዳት ተካፋይ እንድንሆን ስንገደድ ከ “እናውቅላችሗለን” የዘለለ የንቀት መልዕክ የሚያስተላልፈው ቁምነገር ላይኖር ይችላል፡፡ አምደኛው ከቀበሌው ጀምሮ በአካባቢው እና በሃገሩ ጉዳይ ላይ ሲወሰን እና ሲሰለቅ አያገባህም ከተባለ ወሳኙ እና ሰላቂው አካል ሊፈጥረው በሚችለው ስህተትም የሚደርስ ጉዳትን ሊያስወግድለት ይገባል፡፡ ካልሆነ እኛ እንወስን፤ እኛ እንስራ አንተ ደግሞ ትሩፋቱን ተቋደስ ማለት ሊመጣ የሚችለው ትሩፋት ጥቅምም ቢሆን ያልተሳተፈበት ጉዳይ ነውና አያረካውም፡፡ ተሳትፎን ልናረጋግጥባቸው ከምንችላቸው የተለያዩ መንገዶች ደግሞ አንዱ ሃሳብን በተለያዩ መንገዶች መግለጽ ሲሆን በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ ሰዎች ሃሳባችንን እንዲደግፉም ጥሪ ማቅረብ እንችላለን፡፡ ይህ አይሆንም ካሉ ግን “እናውቅላችሗለን” የሚሉት አካላት ያወጡልን እና እንድንቀበለው ያደረጉንን ህግ ለእነሱ ጊዜ እንደማይሰራ እየነገሩን ነው ማለት ነው፡፡ 

እኔስ መጻፍ ለመጀመር ያነሳሳኝ ጉዳይ ምንድ ነው ?

ከላይ ግልፅ እንዳደረኩት በአሁኑ ወቅት ለራስ ደህንነት ሲባል መፃፍ ማቆም እጅግ ተመራጩ ውሳኔ ነው፡፡ ማሻሻያ ሃሳብ መስጠት፣ ትችት መሰንዘር፣ አዲስ ሃሳብ ማቅረብ የመሳሰሉት በአሉታዊ መልኩ ከተተረጎሙ እና ዋጋ የሚያስከፍሉ ሆነው ከተገኙ ዝም ማለቱ የተሻለው አማራጭ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ይህ አማራጭ እጅግ አስከፊ ከሆኑት ምርጫዎች በአንጻራዊ መልኩ አነስ ያለ ጉዳት ያለው አማራጭ ነው እንጂ ጉዳት የለውም አሊያም ዋጋ አያስከፍልም ማለት አይደለም፡፡ መጻፍም አለመጻፍም በዚህች ሃገር ዋጋ ያስከፍላል፡፡ እንዲያውም አለመጻፍ የበለጠ ዋጋ ሊያስከፍል ይችላል፡፡ ልዩነቱ በመጻፋችን የምንከፍለውን ዋጋ የምናውቀው በፍጥነት ሲሆን ባለመጻፋችን የምንከፍለውን ዋጋ የምናውቀው ቀስ በቀስ መሆኑ ነው፡፡ ባለመጻፋችን ወይንም ሃሳባችን ባለመግለጻችን ቀስ በቀስ ቤተሰባችን፣ አካባቢያችን ብሎም ባጠቃላይ ሃገራችን እንደፈለጉ እንዲወስኑ እና እንዲሰልቁ በተፈቀደላቸው አካላት እጅ ስር እንደወደቀች እና በእነሱ መዘዝ እየመጣ ባለው ድህነት፣ የኑሮ ውድነት እና የመሳሰሉት ችግሮችም ሁላችንም ጉዳት ላይ እየወደቅን እንደሆነ እያየን ነው፡፡ 

እኔ እንደምረዳው ለመብቶቻችን እንዲሁም ለነጻነታችን መታገል ማለት ነገሮች እንዲመቻቹልን መጠየቅ ሳይሆን ከምንም ነገር ተነስተን ነገሮችን ማመቻቸት ነው፡፡ የነጻነት ትሩፋት የሚጥመው የሚያስከፍለው ዋጋ የከፋ ስለሆነ ይመስለኛል፡፡ በአድዋ ድል የምንኮራበትን ያህል ድሉን ለማምጣት የተከፈለውን መስዋትነት እና የታለፈውን መንገድ አንዘነጋም፡፡ ሃሳብን የመግለጽ ነጻነት እንዲረጋገጥ እና በነጻነት መጻፍ እንድንችል ማድረግ ያለብን በብዙ ሃሳባችን መግለጽ እና በብዙ መፃፍ ነው፡፡ መፃፍ እንደተከለከልን እና ይሄም ትክክል እንዳልሆነ ልንገልፅ የምንችለው በመጻፍ ነው፡፡ ያሉን ጥቂት ፀሃፍት እንዳይፅፉ ከተከለከሉ እና የሚፅፍ ከጠፋ ማን ችግራችን፣ ብሶታችንን እና ፍላጎታችንን እንዲገልጽልን እንጠብቃለን ? 

በእርግጥ በአሁኑ ወቅት ያለው ሁኔታ በብዙ እንድንጽፍ የሚያስገድድ እንጂ ከመጻፍ እንድንቆጠብ የሚያደርገን አይመስለኝም፡፡ ሰው ስለጻፈ፣ ስለተቸ እና አማራጭ ስላቀረበ “አሸባሪ” ከተባለ ይህ አሸባሪነት አለመሆኑን የምናስረዳው በመጻፍ ነው፡፡ ሰው ተቸግሮ እና ኑሮ ከብዶት “በቃኝ!” ብሎ አደባባይ ሲወጣ “ነውጠኛ” ከተባለ ይህ ነውጠኝነት አለመሆኑን የምናስረዳው በመጻፍ ነው፡፡ ስንቃወም ከተፈረጅን፤ ስንጽፍ ከተጠረጠርን አሁንም በመጻፍ ትክክል አለመሆኑን መግለፅ ይኖርብናል፡፡ የሚጽፉት ሲታሰሩ የታሰሩት እንዲፈቱ መጻፍ አለብን፡፡ አንዱ “መጻፍ የለብህም” ሲባል ሌላው “መጻፍ መብቱ ነው” ብሎ መጻፍ አለበት:: በእርግጥ ይህንን ስንል ወይንም ይህንን ስንጽፍ እኛም ተመሳሳይ እጣ እንደሚደርስብን እርግጥ ነው ነገርግን ምርጫው እጅግ በጣም ቢከፋ ዝም ብሎ ከማለቅ እና ተናግሮ ከማለቅ የትኛው ይሻላል የሚል ነው፡፡ የሃገሬ ብሂል “እውነትን ተናግሮ ከመሸበት ማደር” የሚል ነው እናም እኔ ሃሳቤን ገልጨ የሚመጣውን መጋፈጥ መርጫለሁ፡፡

ስለጻፍኩ ምን ሊመጣብኝ ይችላል?

መጻፍ ስለጀመረኩ ብዙ ችግሮች ሊከተሉብኝ እንደሚችሉ እገምታለሁ፡፡ ለነገሩ በአሁኑ ወቅት በሚጽፉ ጋዜጠኞች እና አምደኞች ዙሪያ እየደረሰ ያለውን ችግር እያየን ስለሆነ ይህ ግምቴ በአብዛኛው ወደ እውነታነት ያጋደለ ነውና “ብዙ ችግሮች ሊከተሉብኝ እንደሚችሉ አውቃለሁ” በሚል አገላለጼን ባስተካክለው ይመረጣል፡፡ በእውነት በአሁኑ ወቅት የጻፈ “አሸባሪ” እየተባለ ነው፡፡ በእርግጥ መጻፍ ሊያሸብር ይችላል፡፡ ነገር ግን መጻፍ ማንን ነው ሊያሸብር የሚችለው? መጻፍ ሊያሸብር የሚችለው በተጻፈበት ጉዳይ ዙሪያ የሚመለከተው አካል ትችቱን ማስተባበል ወይንም መቀበል የማይችል ከሆነ ነው፡፡ ማንኛውም ስራ ከትችት ሊያመልጥ አይችልም ነገር ግን አንድ ተተቺ ሁለት ምርጫዎች አሉት እነሱም ትችቱን በበቂ አመክኖአዊ አቀራረብ ማስተባበል አሊያም ትችቱን መቀበል ናቸው፡፡ ይህ ተተቺ አካል የቀረበበትን ትችት ማስተባበል የማይችል ከሆነ እና ትችቱን ለመቀበል የሚያስችል የሞራል ልዕልና ከሌለው ግን ሊሸበርም በርካታ አሉታዊ ነገሮችን በጽሁፉ እና በጸሃፊው ላይ ሊያስከትልም ይችላል፡፡

ይህ ተተቺ አካል በመጀመሪያ ሊያደርግ የሚችለው ፅሁፉን ማጣጣል እና የጸሃፊውን ስም ማጥፋት ነው፡፡ አንድ ጽሁፉ በደምሳሳው “አፍራሽ” ከተባለ ይህንን ስም የሰጠው አካል እየገነባ ያለው ነገር አለ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ምን እየገነባ እንዳለ እና ይህ ፅሁፍ እንዴት ሊያፈርሰው እንደሚችል አይገልጽም፡፡ ይህ አመክኖአዊ አቀራረብ የሌለው ተራ ስም ማጥፋት እና ጥቁር ጥላ መቀባት ነው፡፡ ቀድሞነገር ተተቺው  የሚገነባው በዚህ ፅሁፍ የሚፈርስ ነገር ከሆነ ከመጀመሪያውም ሲገነባ የነበረው ፈራሽ ነበር ማለት ነው፡፡  

ተተቺው አካል ከስም ማጥፋት ያለፈ ችግር የማስከተል ስልጣን እና ጉልበት ያለው ከሆነ ደግሞ በአሁኑ ወቅት እያየን እንዳለነው “አሸባሪ” ወይንም ሌላ ተለጣፊ ስም ሰጥቶ ሊያስፈራራ፣ ሊከስ እና ሊያስር ይችላል፡፡ ይህ በይበልጥ የሚጎዳው ተችውን ሲሆን ያለስሙ ስም ተሰጥቶት እና ያለጥፋቱ ተከሶ ሊታሰር እና ሊሰቃይ ይችላል፡፡ ከዚህ ባለፈ ደግሞ በዙሪያው ያሉትን ሰዎች እና በሚጽፈው ሃሳብ ምክንያት ብሶታቸውን እየገለጸላቸው ላለው ህዝቦች ጉዳት ነው፡፡ የመገናኛ ብዙሃን ነጻነት ላይም የከፋ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡

ከዚህ ሲከፋ ደግሞ ከሃገር ከማባረር እስከመግደል ሊደርስ ይችላል፡፡ ይህ አሁንም ተቺውን ወይንም ጸሃፊውን (ጋዜጠኛውን) ይበልጥ ተጎጂ ያደርገዋል፡፡ መስዋዕትነቱም የከፋ ነው፡፡ የመገናኛ ብዙሃን ነጻነትም ግባዕተ መሬቱ ሊፈጸም ይችላል፡፡ 

ይሁን እንጂ  እነዚህ ከላይ የተጠቀሱ  ጥቃቶች ሁሉ የሚሰነዘሩት በፀሃፊዎች አሊያም በመገናኛ ብዙሃን ላይ ሲሆን ከዚህ እጅግ እየከፋ ሲሄድ ግን ህጎች፣ ደንቦች እና መመሪያዎች ይበልጥ እንዲጠብቁ እና ጭራሹንም ሃሳብን መግለፅ እንዳይቻል እስከመከልከል ሊደርስ ይችላል፡፡ ይህ ከላይ ለሚፈጸሙ ጥቃቶች ህጋዊ ሽፋን ይሰጣቸዋል፡፡ ይሄ ደግሞ በጠቅላላው የሃገርን እና ህዝብ እድገት የሚጎዳ እና በአንድ አባገነን መሪ ጥላ ስር እንድንበረከክ የሚስገድድ ይሆናል፡፡

ሁሉንም ሊደርሱ የሚችሉ ጥቃቶች ለመከላከል ግን አሁንም መፍትሄው ዙሪያ ገጠም ነው፡፡ ሃሳባችንን መግለጽ እንዳንከለከል ሃሳባችን መግለጽ ይኖርብናል፤ መጻፍ እንዳንከለከል መጻፍ ይኖርብናል፤ መብቶችንን ለማስከበር ለመብቶቻችን መታገል ይኖርብናል፡፡ 
 
ለመሆኑ እኔ ማን ነኝ ?

በሙያየ ጋዜጠኛ ነኝ፡፡ በብሄራዊው የሬድዮ እና የቴሌቪዥን ጣቢያ ከአራት አመት ላላነሰ ግዜ ሰርቻለሁ፡፡ በመጀመሪያዎቹ ሁለት አመት ከመንፈቅ የሚሆኑ ጊዜያት በብሄራዊ ሬድዮ ጣቢያ የሰራሁ ሲሆን ከእነዚህ ግዜያት ውስጥም በመጀመሪያዎቹ ወቅቶች በተሻለ ነጻነት ስሰራ ቆይቻለሁ፡፡ ቀስ በቀስ ጉዳዮች እየጠነከሩ እና “ልማታዊው” የጋዜጠኛ ሰራዊት እያየለ ሲመጣ በነጻነት መስራት የሚለው ጉዳይ እየከበደኝ እና ሌላው ቀርቶ ሙያዊ በሆኑ ጉዳዮች መግባባት እየተሳነኝ መጣሁ፡፡ በብሄራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያው በቆየሁባቸው ጥቂት ጊዜያትም የተለያዩ ማሕበራዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ፕሮግራሞችን የሰራሁ ቢሆንም በተጽኖ ስር ነው የቆየሁት፡፡ ከዚያ በሗላ ድርጅቱን ለቅቄ አንድ አድቮኬሲ ላይ የሚሰራ ህዝባዊ ማህበር ውስጥ ተቀጥሬ ለአንድ አመት ስሰራ ቆይቻለሁ፡፡ በዚህ ወቅትም በተለይ ከህዝብ እና ከግሉ የመገኛኝ ብዙሃን ጋዜጠኞች ጋር በቅርበት የሰራሁ ሲሆን ብዙም ግንዛቤ ያልነበረኝን መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን አሰራር እና እንቅስቃሴም በቅርበት ለመከታተል ችያለሁ፡፡ ከሁሉም በበለጠ ግን ይህ ግዜ ለእኔ የአርምሞ ግዜ ነበር፡፡
በዙሪያየ ያሉት በርካታዎቹ ሰዎች ጋዜጠኞች አሊያም ሙያውን የተማሩ ስለሆኑ በአንድ አንድ በሚያብሰከስኩኝ ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ስንወያይ “ለምን አትፅፍም?” እያሉ ይወተውቱኛል፡፡ እርግጥ ነው ልጽፍ የምችልባቸው ርዕሰ ጉዳዮች ነበሩኝ ነገር ግን በእነዚህ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ምን ያህል የተሻለ መረጃ እና ግንዛቤ አለኝ? ብሎም እነዚህን ጉዳዮች ምን ያህል አመክኖአዊ አቀራረብ ባለው መልኩ ልተነትናቸው እችላለሁ የሚለው ነበር ስጋቴ፡፡ ከጓደኞቼ የገጠመኝ ትልቁ መከራከሪያ ነጥብ ግን እነዚህን ሃሳቦቼን ዘርዝሬ ካላቀረብኳቸው ትክክል ስለመሆኔ እና ስለመሳሳቴ ማስረጃ እንደሌለ ነው፡፡ ከዚህም ባለፈ ከላይ እንዳሰፈርኩት ካልተተቸሁ ልማር እንደማልችል አምናለሁ፡፡ በዚህም ምክንያት መጻፍ ለመጀመር ሃሳቦቼን ሳደራጅ እና መረጃዎችን ስሰበስብ ጊዜ ፈጅቶብኛል፡፡ በዚህ ጊዜ የተገነዘብኩትን ጉዳይ ለመግለፅ ግን መጻፍ ያልጀመርኩት በእውነትም ፈርቼ ስለነበር ነው፡፡ አንድም ጥቃት እንዳይሰነዘርብኝ ፈርቼ ነበር ፤ አንድም የሰላ ትችት እንዳይሰነዘርብኝ ፈርቼ ነበር፡፡ 

ከዚህ ባለፈ ልጽፍ በምችለው ነገር ከስሜታዊነት ለመጽዳት እና ሰዎችን ላለመወንጀል ጥረት አደርጋለሁ፡፡ መረጃዎቼ በአስተያየት እና በእውነታ ላይ የተመሰረቱ እንዲሆን እና ልሰጥ የምችለው ትንታኔ ከእነዚህ የተነሳ እንዲሆን ሙያየም ያስገድደኛል፡፡