ፋሲለደስ

ፋሲለደስ

Tuesday, November 22, 2011

መፃፍ ጀምሬያለሁ

ከቅርብ ጊዜያት በፊት በአውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ላይ ሲጽፍ የቆየ አምደኛ “መፃፍ አቁሜያለሁ” በሚል ርዕስ አንድ ጠንከር ያለ አመክኖ ያለው የጽሁፍ ሃተታ አቅርቦ መጻፍ አቆመ፡፡ ይህንን ጽሁፍ ካንብበኩ በሗላ መፃፍ ብፈልግም መፃፍ ለመጀመር ብዙ ጊዜ ፈጀብኝ፡፡ ሆኖም መጻፍ ለመጀመር የቆሰቆሰኝ ዋናው ጉዳይ ይሄው ሲሆን አምደኛው መፃፍ ካቆመ በሓላ እንኳ ባለፉት ጊዜያት የሆኑት ጉዳዮች ደግሞ መፃፍ ለመጀመር ፈራ ተባ እያልኩ እንድቆይ አስገድደውኝ ሰንብተዋል፡፡ 

በእርግጥ አምደኛው መፃፍ ለማቆም የተገደደበት ዋናው ጉዳይ ምን ነበር ? 

አምደኛው በየሳምነቱ በሚፅፋቸው ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማሕበራዊ ጉዳዮችን በሚተነትኑ እና በሚተቹ ፅሁፎቹ ምክንያት ያልተደሰቱ ወገኖች እንዳይፅፍ እንቅፋት ሆኑበት፡፡ ዛቻ እና ማስፈራራት ሲያበዙበት እና በአንድም ሆነ በሌላ ምክንያት በህጋዊው መንገድ ሄዶ ሊያሸንፋቸው እንደማይችል ሲገምት እነዚህን ያልተደሰቱ ወገኖች ማስደሰት የሚቻልበት ብቸኛው አማራጭ መጻፍ በማቆም ብቻ እንደሆነ አመነ፡፡ እናም መፃፍ አቆመ፡፡ እሱ ሰላም ለማግኘት ሲል ወይንም ወህኒ ቤት እንዳይወረወር አሊያም ሕይወቱን ለማቆየት መጻፍ ማቆሙ ትክክል ነበር፡፡  

ነገር ግን ይህ አምደኛ መጻፍ በማቆሙም እርሱ እንደገለጸልን በሁለት ነገሮች ተጎዳ፤ አንድም በሕገ መንግስቱ ዋስትና ተሰቶት የነበረውን ሃሳቡን የመግለጽ ነጻነቱን ተገፈፈ፤ አንድም በመጻፍ ያገኝ የነበረው ገቢ ተቋረጠ፡፡ በእኔ እምነት የመጀመሪያው ጉዳት እጅግ የከፋ ነው ምክንያቱም በራሱ ሃገር እና በራሱ ጉዳይ ላይ የራሱ ሃገር ሰዎች ሲወስኑ እና ያሻቸውን ሲተገብሩ ዝም ብሎ መመልከትን የመሰለ የሚያስከፋ ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ መንግስትም ሆነ በተዋረድ ያሉ አካላት በሚያቀርቡት ሃሳብ ላይ ተጨማሪ ሃሳብ ማቅረብ ፣ ማስተካከያ ሃሳብ መሰንዘር፣ መተቸት እና መቃወም ሲቻል የቀረበው ሃሳብ እንደወረደ ተወስኖ እና ተተግብሮ ሊያደርስ የሚያስችለውን ጥቅምም ሆነ ጉዳት ተካፋይ እንድንሆን ስንገደድ ከ “እናውቅላችሗለን” የዘለለ የንቀት መልዕክ የሚያስተላልፈው ቁምነገር ላይኖር ይችላል፡፡ አምደኛው ከቀበሌው ጀምሮ በአካባቢው እና በሃገሩ ጉዳይ ላይ ሲወሰን እና ሲሰለቅ አያገባህም ከተባለ ወሳኙ እና ሰላቂው አካል ሊፈጥረው በሚችለው ስህተትም የሚደርስ ጉዳትን ሊያስወግድለት ይገባል፡፡ ካልሆነ እኛ እንወስን፤ እኛ እንስራ አንተ ደግሞ ትሩፋቱን ተቋደስ ማለት ሊመጣ የሚችለው ትሩፋት ጥቅምም ቢሆን ያልተሳተፈበት ጉዳይ ነውና አያረካውም፡፡ ተሳትፎን ልናረጋግጥባቸው ከምንችላቸው የተለያዩ መንገዶች ደግሞ አንዱ ሃሳብን በተለያዩ መንገዶች መግለጽ ሲሆን በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ ሰዎች ሃሳባችንን እንዲደግፉም ጥሪ ማቅረብ እንችላለን፡፡ ይህ አይሆንም ካሉ ግን “እናውቅላችሗለን” የሚሉት አካላት ያወጡልን እና እንድንቀበለው ያደረጉንን ህግ ለእነሱ ጊዜ እንደማይሰራ እየነገሩን ነው ማለት ነው፡፡ 

እኔስ መጻፍ ለመጀመር ያነሳሳኝ ጉዳይ ምንድ ነው ?

ከላይ ግልፅ እንዳደረኩት በአሁኑ ወቅት ለራስ ደህንነት ሲባል መፃፍ ማቆም እጅግ ተመራጩ ውሳኔ ነው፡፡ ማሻሻያ ሃሳብ መስጠት፣ ትችት መሰንዘር፣ አዲስ ሃሳብ ማቅረብ የመሳሰሉት በአሉታዊ መልኩ ከተተረጎሙ እና ዋጋ የሚያስከፍሉ ሆነው ከተገኙ ዝም ማለቱ የተሻለው አማራጭ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ይህ አማራጭ እጅግ አስከፊ ከሆኑት ምርጫዎች በአንጻራዊ መልኩ አነስ ያለ ጉዳት ያለው አማራጭ ነው እንጂ ጉዳት የለውም አሊያም ዋጋ አያስከፍልም ማለት አይደለም፡፡ መጻፍም አለመጻፍም በዚህች ሃገር ዋጋ ያስከፍላል፡፡ እንዲያውም አለመጻፍ የበለጠ ዋጋ ሊያስከፍል ይችላል፡፡ ልዩነቱ በመጻፋችን የምንከፍለውን ዋጋ የምናውቀው በፍጥነት ሲሆን ባለመጻፋችን የምንከፍለውን ዋጋ የምናውቀው ቀስ በቀስ መሆኑ ነው፡፡ ባለመጻፋችን ወይንም ሃሳባችን ባለመግለጻችን ቀስ በቀስ ቤተሰባችን፣ አካባቢያችን ብሎም ባጠቃላይ ሃገራችን እንደፈለጉ እንዲወስኑ እና እንዲሰልቁ በተፈቀደላቸው አካላት እጅ ስር እንደወደቀች እና በእነሱ መዘዝ እየመጣ ባለው ድህነት፣ የኑሮ ውድነት እና የመሳሰሉት ችግሮችም ሁላችንም ጉዳት ላይ እየወደቅን እንደሆነ እያየን ነው፡፡ 

እኔ እንደምረዳው ለመብቶቻችን እንዲሁም ለነጻነታችን መታገል ማለት ነገሮች እንዲመቻቹልን መጠየቅ ሳይሆን ከምንም ነገር ተነስተን ነገሮችን ማመቻቸት ነው፡፡ የነጻነት ትሩፋት የሚጥመው የሚያስከፍለው ዋጋ የከፋ ስለሆነ ይመስለኛል፡፡ በአድዋ ድል የምንኮራበትን ያህል ድሉን ለማምጣት የተከፈለውን መስዋትነት እና የታለፈውን መንገድ አንዘነጋም፡፡ ሃሳብን የመግለጽ ነጻነት እንዲረጋገጥ እና በነጻነት መጻፍ እንድንችል ማድረግ ያለብን በብዙ ሃሳባችን መግለጽ እና በብዙ መፃፍ ነው፡፡ መፃፍ እንደተከለከልን እና ይሄም ትክክል እንዳልሆነ ልንገልፅ የምንችለው በመጻፍ ነው፡፡ ያሉን ጥቂት ፀሃፍት እንዳይፅፉ ከተከለከሉ እና የሚፅፍ ከጠፋ ማን ችግራችን፣ ብሶታችንን እና ፍላጎታችንን እንዲገልጽልን እንጠብቃለን ? 

በእርግጥ በአሁኑ ወቅት ያለው ሁኔታ በብዙ እንድንጽፍ የሚያስገድድ እንጂ ከመጻፍ እንድንቆጠብ የሚያደርገን አይመስለኝም፡፡ ሰው ስለጻፈ፣ ስለተቸ እና አማራጭ ስላቀረበ “አሸባሪ” ከተባለ ይህ አሸባሪነት አለመሆኑን የምናስረዳው በመጻፍ ነው፡፡ ሰው ተቸግሮ እና ኑሮ ከብዶት “በቃኝ!” ብሎ አደባባይ ሲወጣ “ነውጠኛ” ከተባለ ይህ ነውጠኝነት አለመሆኑን የምናስረዳው በመጻፍ ነው፡፡ ስንቃወም ከተፈረጅን፤ ስንጽፍ ከተጠረጠርን አሁንም በመጻፍ ትክክል አለመሆኑን መግለፅ ይኖርብናል፡፡ የሚጽፉት ሲታሰሩ የታሰሩት እንዲፈቱ መጻፍ አለብን፡፡ አንዱ “መጻፍ የለብህም” ሲባል ሌላው “መጻፍ መብቱ ነው” ብሎ መጻፍ አለበት:: በእርግጥ ይህንን ስንል ወይንም ይህንን ስንጽፍ እኛም ተመሳሳይ እጣ እንደሚደርስብን እርግጥ ነው ነገርግን ምርጫው እጅግ በጣም ቢከፋ ዝም ብሎ ከማለቅ እና ተናግሮ ከማለቅ የትኛው ይሻላል የሚል ነው፡፡ የሃገሬ ብሂል “እውነትን ተናግሮ ከመሸበት ማደር” የሚል ነው እናም እኔ ሃሳቤን ገልጨ የሚመጣውን መጋፈጥ መርጫለሁ፡፡

ስለጻፍኩ ምን ሊመጣብኝ ይችላል?

መጻፍ ስለጀመረኩ ብዙ ችግሮች ሊከተሉብኝ እንደሚችሉ እገምታለሁ፡፡ ለነገሩ በአሁኑ ወቅት በሚጽፉ ጋዜጠኞች እና አምደኞች ዙሪያ እየደረሰ ያለውን ችግር እያየን ስለሆነ ይህ ግምቴ በአብዛኛው ወደ እውነታነት ያጋደለ ነውና “ብዙ ችግሮች ሊከተሉብኝ እንደሚችሉ አውቃለሁ” በሚል አገላለጼን ባስተካክለው ይመረጣል፡፡ በእውነት በአሁኑ ወቅት የጻፈ “አሸባሪ” እየተባለ ነው፡፡ በእርግጥ መጻፍ ሊያሸብር ይችላል፡፡ ነገር ግን መጻፍ ማንን ነው ሊያሸብር የሚችለው? መጻፍ ሊያሸብር የሚችለው በተጻፈበት ጉዳይ ዙሪያ የሚመለከተው አካል ትችቱን ማስተባበል ወይንም መቀበል የማይችል ከሆነ ነው፡፡ ማንኛውም ስራ ከትችት ሊያመልጥ አይችልም ነገር ግን አንድ ተተቺ ሁለት ምርጫዎች አሉት እነሱም ትችቱን በበቂ አመክኖአዊ አቀራረብ ማስተባበል አሊያም ትችቱን መቀበል ናቸው፡፡ ይህ ተተቺ አካል የቀረበበትን ትችት ማስተባበል የማይችል ከሆነ እና ትችቱን ለመቀበል የሚያስችል የሞራል ልዕልና ከሌለው ግን ሊሸበርም በርካታ አሉታዊ ነገሮችን በጽሁፉ እና በጸሃፊው ላይ ሊያስከትልም ይችላል፡፡

ይህ ተተቺ አካል በመጀመሪያ ሊያደርግ የሚችለው ፅሁፉን ማጣጣል እና የጸሃፊውን ስም ማጥፋት ነው፡፡ አንድ ጽሁፉ በደምሳሳው “አፍራሽ” ከተባለ ይህንን ስም የሰጠው አካል እየገነባ ያለው ነገር አለ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ምን እየገነባ እንዳለ እና ይህ ፅሁፍ እንዴት ሊያፈርሰው እንደሚችል አይገልጽም፡፡ ይህ አመክኖአዊ አቀራረብ የሌለው ተራ ስም ማጥፋት እና ጥቁር ጥላ መቀባት ነው፡፡ ቀድሞነገር ተተቺው  የሚገነባው በዚህ ፅሁፍ የሚፈርስ ነገር ከሆነ ከመጀመሪያውም ሲገነባ የነበረው ፈራሽ ነበር ማለት ነው፡፡  

ተተቺው አካል ከስም ማጥፋት ያለፈ ችግር የማስከተል ስልጣን እና ጉልበት ያለው ከሆነ ደግሞ በአሁኑ ወቅት እያየን እንዳለነው “አሸባሪ” ወይንም ሌላ ተለጣፊ ስም ሰጥቶ ሊያስፈራራ፣ ሊከስ እና ሊያስር ይችላል፡፡ ይህ በይበልጥ የሚጎዳው ተችውን ሲሆን ያለስሙ ስም ተሰጥቶት እና ያለጥፋቱ ተከሶ ሊታሰር እና ሊሰቃይ ይችላል፡፡ ከዚህ ባለፈ ደግሞ በዙሪያው ያሉትን ሰዎች እና በሚጽፈው ሃሳብ ምክንያት ብሶታቸውን እየገለጸላቸው ላለው ህዝቦች ጉዳት ነው፡፡ የመገናኛ ብዙሃን ነጻነት ላይም የከፋ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡

ከዚህ ሲከፋ ደግሞ ከሃገር ከማባረር እስከመግደል ሊደርስ ይችላል፡፡ ይህ አሁንም ተቺውን ወይንም ጸሃፊውን (ጋዜጠኛውን) ይበልጥ ተጎጂ ያደርገዋል፡፡ መስዋዕትነቱም የከፋ ነው፡፡ የመገናኛ ብዙሃን ነጻነትም ግባዕተ መሬቱ ሊፈጸም ይችላል፡፡ 

ይሁን እንጂ  እነዚህ ከላይ የተጠቀሱ  ጥቃቶች ሁሉ የሚሰነዘሩት በፀሃፊዎች አሊያም በመገናኛ ብዙሃን ላይ ሲሆን ከዚህ እጅግ እየከፋ ሲሄድ ግን ህጎች፣ ደንቦች እና መመሪያዎች ይበልጥ እንዲጠብቁ እና ጭራሹንም ሃሳብን መግለፅ እንዳይቻል እስከመከልከል ሊደርስ ይችላል፡፡ ይህ ከላይ ለሚፈጸሙ ጥቃቶች ህጋዊ ሽፋን ይሰጣቸዋል፡፡ ይሄ ደግሞ በጠቅላላው የሃገርን እና ህዝብ እድገት የሚጎዳ እና በአንድ አባገነን መሪ ጥላ ስር እንድንበረከክ የሚስገድድ ይሆናል፡፡

ሁሉንም ሊደርሱ የሚችሉ ጥቃቶች ለመከላከል ግን አሁንም መፍትሄው ዙሪያ ገጠም ነው፡፡ ሃሳባችንን መግለጽ እንዳንከለከል ሃሳባችን መግለጽ ይኖርብናል፤ መጻፍ እንዳንከለከል መጻፍ ይኖርብናል፤ መብቶችንን ለማስከበር ለመብቶቻችን መታገል ይኖርብናል፡፡ 
 
ለመሆኑ እኔ ማን ነኝ ?

በሙያየ ጋዜጠኛ ነኝ፡፡ በብሄራዊው የሬድዮ እና የቴሌቪዥን ጣቢያ ከአራት አመት ላላነሰ ግዜ ሰርቻለሁ፡፡ በመጀመሪያዎቹ ሁለት አመት ከመንፈቅ የሚሆኑ ጊዜያት በብሄራዊ ሬድዮ ጣቢያ የሰራሁ ሲሆን ከእነዚህ ግዜያት ውስጥም በመጀመሪያዎቹ ወቅቶች በተሻለ ነጻነት ስሰራ ቆይቻለሁ፡፡ ቀስ በቀስ ጉዳዮች እየጠነከሩ እና “ልማታዊው” የጋዜጠኛ ሰራዊት እያየለ ሲመጣ በነጻነት መስራት የሚለው ጉዳይ እየከበደኝ እና ሌላው ቀርቶ ሙያዊ በሆኑ ጉዳዮች መግባባት እየተሳነኝ መጣሁ፡፡ በብሄራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያው በቆየሁባቸው ጥቂት ጊዜያትም የተለያዩ ማሕበራዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ፕሮግራሞችን የሰራሁ ቢሆንም በተጽኖ ስር ነው የቆየሁት፡፡ ከዚያ በሗላ ድርጅቱን ለቅቄ አንድ አድቮኬሲ ላይ የሚሰራ ህዝባዊ ማህበር ውስጥ ተቀጥሬ ለአንድ አመት ስሰራ ቆይቻለሁ፡፡ በዚህ ወቅትም በተለይ ከህዝብ እና ከግሉ የመገኛኝ ብዙሃን ጋዜጠኞች ጋር በቅርበት የሰራሁ ሲሆን ብዙም ግንዛቤ ያልነበረኝን መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን አሰራር እና እንቅስቃሴም በቅርበት ለመከታተል ችያለሁ፡፡ ከሁሉም በበለጠ ግን ይህ ግዜ ለእኔ የአርምሞ ግዜ ነበር፡፡
በዙሪያየ ያሉት በርካታዎቹ ሰዎች ጋዜጠኞች አሊያም ሙያውን የተማሩ ስለሆኑ በአንድ አንድ በሚያብሰከስኩኝ ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ስንወያይ “ለምን አትፅፍም?” እያሉ ይወተውቱኛል፡፡ እርግጥ ነው ልጽፍ የምችልባቸው ርዕሰ ጉዳዮች ነበሩኝ ነገር ግን በእነዚህ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ምን ያህል የተሻለ መረጃ እና ግንዛቤ አለኝ? ብሎም እነዚህን ጉዳዮች ምን ያህል አመክኖአዊ አቀራረብ ባለው መልኩ ልተነትናቸው እችላለሁ የሚለው ነበር ስጋቴ፡፡ ከጓደኞቼ የገጠመኝ ትልቁ መከራከሪያ ነጥብ ግን እነዚህን ሃሳቦቼን ዘርዝሬ ካላቀረብኳቸው ትክክል ስለመሆኔ እና ስለመሳሳቴ ማስረጃ እንደሌለ ነው፡፡ ከዚህም ባለፈ ከላይ እንዳሰፈርኩት ካልተተቸሁ ልማር እንደማልችል አምናለሁ፡፡ በዚህም ምክንያት መጻፍ ለመጀመር ሃሳቦቼን ሳደራጅ እና መረጃዎችን ስሰበስብ ጊዜ ፈጅቶብኛል፡፡ በዚህ ጊዜ የተገነዘብኩትን ጉዳይ ለመግለፅ ግን መጻፍ ያልጀመርኩት በእውነትም ፈርቼ ስለነበር ነው፡፡ አንድም ጥቃት እንዳይሰነዘርብኝ ፈርቼ ነበር ፤ አንድም የሰላ ትችት እንዳይሰነዘርብኝ ፈርቼ ነበር፡፡ 

ከዚህ ባለፈ ልጽፍ በምችለው ነገር ከስሜታዊነት ለመጽዳት እና ሰዎችን ላለመወንጀል ጥረት አደርጋለሁ፡፡ መረጃዎቼ በአስተያየት እና በእውነታ ላይ የተመሰረቱ እንዲሆን እና ልሰጥ የምችለው ትንታኔ ከእነዚህ የተነሳ እንዲሆን ሙያየም ያስገድደኛል፡፡     

4 comments:

muluken said...

Fasilo metafe herif neger new min gizam yetaxrga menged eshohe ena enkefat layenor yechelal. Ante gen ba yetaxaraga meged laye ka megoaz yaletaxaragawen menged falegahe be eshohena be enkefat wesete eyahadek betadege yeteshale neger tefateralehe.

tsegafm said...

Fasildes i thought you were kidding when you said ''I’m gone start writing". Now i have to tell you, this is a great beginning. And if I may scrounge Neil Armstrong’s saying that seems to be one small step for an individual, but it is indeed one giant leap for the profession of writing in that great land. My friend, keep up the good work. And pleas look after yourself.

Selina said...

I really appreciate the intention and courage that makes you design this blog Fasil. One thing I would like to suggest is, it would make the blog more interesting if you welcome others to input their thoughts and allow discussions too; as you said a balanced one.
Keep going dear; I am proud of you^^

coca said...

fasilo mengedun cherq yadirglih tsaf enanebalen...ketaserk enditfeta metsaf enjemiralen...

Post a Comment