Saturday, April 8, 2023

ፕሮፓጋንዳ እንዴት ይሰራል

ፕሮፖጋንዳ ከየትኛዉም ዘመናዊ የጦር መሳሪያ የበለጠ ሀይል ያለዉ እና አንድን ዒላማ ያደረገበትን የህብረተሰብ ክፍል ሊያከሽፍ እና መልሶ ለራሱ ዓላማ መጠቀሚያ ሊያደርግ የሚችል መሳሪያ ነዉ።   
ዉጤታማ ፕሮፖጋንዳ ማለት ይህ ዒላማ የተደረገበት የህብረተሰብ ክፍል የያዘዉ አቋም አሊያም እዉነት ነዉ ብሎ የተቀበለዉ ሀሳብ በፕሮፓጋንዲስቱ ጫና ያልመጣ መስሎ ሲሰማዉ እና እራሱ አንፃራዊ ሁኔታዎችን መርምሮ የደረሰበት መደምደሚያ እንደሆነ ሲገምት ነዉ።  
ይህን አይነት "ዉጤታማ" የፕሮፓጋንዳ ስትራቴጂ ለመተግበር ፕሮፓጋንዲስቱ በቅድሚ የዚህን ዒላማ ያደረገበትን የህብረተሰብ ክፍል ማንነት እና ምንነት ያጠናል፤ ደካማ እና ጠንካራ ጎኑን ይፈትሻል፤ የመረጃ ምንጬን፣ መረጃዉን የሚያገኝበትን መንገድ እና መረብ ይመረምራል።  
ከዚህ ጥናት በኃላ በምን መልክ ምን መረጃ እንዴት ማቅረብ እንዳለበት እና ለምን ዓላማ ይህ ሊሆን እንደሚችል ይለያል።  
በተለያየ መንገድ ማለትም በመጽሀፍ፣ በምርምር መልክ፣ በትምህርት፣ በመገናኛ ብዙሀን፣ እናም በግለሰብ ደረጃ ፕሮፖጋንዳ ሊዛመት ይችላል 
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ላይ የተቃጣዉ አሉታዊ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ረቂቅነትም ከዚህ የቆዬ ጥናት የመነጨ ነዉ። 
የሚቀርብልህን መረጃ መጠየቅ ካልቻልክ፣ በጥቅሉ እዉነት ነዉ ብለህ ከተቀበልከዉ ተሸንፈሀል።  እርግጥ ነዉ ትምህርት በከፍተኛ ደረጃ ንግድ እየሆነ በመጣበት በአሁኑ ዘመን ለእንደኛ ላለ ተራ የህብረተሰብ ክፍል ሁሉንም ለመመርመር የሚያስችል ማስረጃ ለማግኘት እና ይህንንም መንገድ ለመከተል ጊዜም ገንዘብም ይጠይቃል።
ነገር ግን መሰረታዊ የመጠየቅ ክህሎት ካዳበርክ ጉዳዩን ከስረ መሰረቱ ባትደርስበትም እንኳ በጥርጣሬ እንድትመለከተዉ ይረድሀል። 
ለምሳሌ ያህል በኢትዮጵያ ጉዳይ አንድ ዉሱን የምታምነዉን አቋም በጥቅሉ እንዉሰድ፣ ይሄን አቋምህን እንዴት እና በምን መረጃ ላይ ተመስርተህ ልትደግፍ ቻልክ? ለዚህ አቋምህ እዉነት ያልካቸዉን የመረጃ ምንጮች ከየት እና በምን መንገድ አገኘህ? እነዚህ የመረጃ ምንጮችህ የኋላ ታሪክ ምንድን ነዉ? ይህ የያዝከዉ አቋምህ ከሌላዉ ኢትዬጵያዊነትን በተመለከተ ካለዉ መሰረታዊ አቋምህ በምን መልኩ ይቃረናል ወይንስ ይታረቃል? ይሄን ፕሮፖጋንዳ በግልጽም በሽፋንም የሚያቀብሉህ አካላት የወሰድከዉን አቋም ተከትለህ ምን እንድታደርግ ነዉ የሚፈልጉት ? ይሄን መጠየቅ እና መመርመር ከቻልክ አይንህ እየተገለጠ እና እየሆነ ያለዉን እየተረዳህ ትሄዳለህ። 
የሚባለዉ እና በመሬት ላይ ያለዉን ነገር አነፃጽሮ እየሆነ ያለዉን መለየቱ ላይ ነዉ ቁም ነገሩ። 
ሰላም አሰፍናለሁ ያለህ ሁሉ የሰላም ዘብ ላይሆን ይችላል፤ የዴሞክራሲ ማማ ነኝ የሚልህ ሀገር እና መንግስት ሁሉ የሚለዉ እና እየሆነ ያለዉ የተለያየ ነገር ሊሆን ይችላል፤ አንድነትህን ላስጠብቅልህ የሚልህ ሁሉ የበለጠ ሊበትንህ ይችላል። አሊያም ነጻነት አመጣልሀለሁ ወይንም አመጣሁልህ ያለህ ሁሉ በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ የባርነት ቀንበር ሊያጠልቅልህ እያመቻቸህ ሊሆን ይችላል።  ነፍሱን ለመታደግ እርዳታ የሚያስፈልገዉ ህዝብ እና መንግስት የቁስ እና የገንዘብ እርዳታ ለጋሽ ነኝ እያለ ሀገርህን ሊዘርፍህ ሲዳዳ ካመንክዉ ችግር ነዉ። 
አንተ በትክክል ምንድን ነዉ የምትፈልገዉ? ይሄ ፍላጎትህ እንዴት እና ከየት መጣ?  ፍላጎትህ እና ተግባርህ እንዴት ይግባባል? ይሄን መርምር እንጂ ጠበቃህ ነኝ ያለህ ሁሉ ለክስ እያመቻቸህ እንዳይሆን ተጠንቀቅ። 
ፕሮፓጋንዳ ሁሉ መጥፎ አላማ አለዉ ሊባል ባይችልም እንዲህ ኢትዬጵያ ላይ እንደተቃጣዉ ያለ እንደ ምስጥ ውስጣችንን ሰርስሮ ለመጣል የደረሰ አደገኛ ነገር የለም።  
እጅግ አደገኛ የሚያደርገዉ ደግሞ በአጠቃላይ በህልዉናችን የመጣ እና ሳናዉቀዉ የዚኽዉ የህልዉናችን ማጥፊያ መሳሪያ እና ሰለባ መሆናችን ነዉ።  
የፕሮፖጋንዲስት አላማ አዉቀኽዉም ሆነ ሳታዉቅ እንድትከተለዉ እና ለፈለገዉ ግብ መሳካት መሳሪያ እንድትሆነዉ ማድረግ ነዉ።  ከዚያ በኋላ አንተ ላይ ስለሚፈጠር ተፅዕኖ ሀላፊነት አይወስድም። 
ይሄንን የቆዬ የፕሮፖጋንዳ ዘመቻ ለመቋቋም የግድ ተቋማዊ የሆነ የካዉንተር ፕሮፖጋንዳ እና ኢንዶክትሬኔሽን ማዕከል በግልጽም ሆነ በሽፋን ሀገሪቱ ማቋቋም ያስፈልጋታል። ምክንያቱም በግለሰብ ደረጃ ይሄን ሁሉ ከብረት የከበደ የፕሮፖጋንዳ ናዳ ተቋቁሞ እና ተከላክሎ መቆም አይቻልም።

የአሜሪካ ወዳጅም ጠላትም መሆን አደጋው ብዙ መሆኑን ያለፉት የቅርብ ጊዜ የበርካታ ሃገራት ታሪክ በግልፅ ያሳያል።

የቀዝቃዛው ጦርነት እጅግ በተጋጋለበት የ1960ዎቹ መጨረሻ እና የ1970ዎቹ ዓመታት ወቅት እጅግ አወዛጋቢ አና በአሜሪካ የዉጭ ጉዳይ ፖሊሲ ከባድ ተፅዕኖ ፈጣሪ የነበረዉ ሄነሪ ኪሲንጀር በፖለቲካ ልሂቃን ዘንድ በተደጋጋሚ የሚወሳለት አንድ ድንቅ እውነት ተናግሯል።
ይሄውም "የአሜሪካ ጠላት መሆን አደገኛ ሊሆን ይችላል፤ የአሜሪካ ወዳጅ መሆን ግን በርግጠኝነት አጥፊ (ገዳይ) ነው" የሚለው ንግግሩ ነዉ።
"To be an enemy of America can be dangerous, but to be a friend is fatal. Henry Kissinger
ሄነሪ ኪሲንጀር በ1970ዎቹ በተለያዩ የኤዢያ፣ የአፍሪካ እና የደቡብ አሜሪካ ሃገራት አሜሪካ ታካሂድ በነበረው ጣልቃ ገብነት፣ የኮንቨርት እና ኦቨርት ስራ፣ የመንግስት ግልበጣ እና በርካታ  ቀጥተኛ እና የእጅ አዙር ጦርነቶች ዋና አርቃቂ እና ተዋናይ ስለነበረ ይሄ ንግግሩ ትልቅ ግምት የሚሰጠው ነው።
የአሜሪካ ወዳጅም ጠላትም መሆን አደጋው ብዙ መሆኑን ያለፉት የቅርብ ጊዜ የበርካታ ሃገራት ታሪክ በግልፅ ያሳያል። 
ወዳጅም ጠላትም ሳይሆኑ ኒዉትራል አቋም ይዞ መቆየቱ ላይ ነዉ ትልቁ ጥበብ። ይሄም ቢሆን እንደየሃገራቱ ፍላጎት ብቻ ላይወሰን ይችላል።
አንድ ሃገር ከአሜሪካ ጋር ያላትን ግንኙነት ለመወሰን ካላት አቅም በበለጠ አሜሪካ ከሃገሯ ጋር ያላትን ግንኙነት ለመወሰን ያላት ፍላጎት የበለጠ ተፅዕኖ አለው ።
ግኑኝነቱ በወዳጅነትም ሆነ በጠላትነት ይህ ግንኙነት ይዞት የሚመጣውን መዘዝ የሚከፍለው ግን የዛች ሃገር ህዝብ እና መንግስት ነው።
እንደ ኢትዮጵያ አይነት ትንሽ እና ደካማ ሃገር አሜሪካን ከመሰለ ግዙፍ እና እጀ ረዥም ሃገር ጋር የሚኖራት/ያላት ግንኙነት እንደ አሜሪካ ፍላጎት እና ሃገሪቱ በምታስቀምጠው ህግ እና ደምብ  እንዲሁም ቅርፅ እና ማዕቀፍ መሆኑ እሙን ነው። 
አሜሪካ ካላት አለም ዓቀፍ ተፅኖ የመፍጠር አቅም፣ እጅግ የተጋነነ ሃብት እና ቴክኖሎጂ ምንጭነት እና ወታደራዊ አቅም አንፃር ከሃገሪቱ ጋር በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ ግንኙነት ሳይፈጥሩ ተገልሎ መኖር ይከብዳል።
ነገር ግን የአንድን ሃገር ዉሰጣዊ ጉዳይ ባሻት መልኩ በዲፕሎማሲም ሆነ በሌላ መልኩ ጣልቃ እንድትገባ እና ዉሳኔ ሰጪ አካል እንድትሆን መፍቀድ ይሄን ከመሰለው ግንኙነት ሊገኝ ከታሰበዉ ጥቅም ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል።
የኢትዬጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር  ዶ/ር አብይ አህመድ በአሜሪካ በጎ ፈቃድ ስልጣን ላይ የወጣ መሆኑ ግልፅ የወጣ ነገር ቢሆንም በዚህ ውለታ የአድር ባይነት ባህሪውን ማጠናከሩ ዞሮ ዞሮ ህዝብ እና ሃገር እየጎዳ መሆኑን እያየን ነው። 
በተቃርኖ ጎን የቆመው እና የመንግስቱ ተገዳዳሪ ህውሃትም የአሜሪካ ተልኮ አስፈፃሚ ሆኖ መቅረቡ ችግሩን የበለጠ አወሳስቦታል።
አሁን ያለዉ የአለም ፖለቲካ እየከረረ መምጣት እና የቀዝቃዛው ጦርነት እንደገና ማገርሸት ደግሞ የኢትዬጵያን መንግስት በግልፅ ወገን ለይቶ እንዲቆም የሚያስገድደው ጊዜ እየመጣ ይመስላል። 
አሁን ካለዉ የመንግስታችን ግንኙነት እና አካሄድ መንግስት አጣብቂኝ ውስጥ የገባ እና ሳይወድ ተገዶ የአሜሪካን ጎራ የመረጠ ይመስላል።
ይህ ደግሞ ሊጠጋግነው ጀማምሮት የነበረውን ከኤርትራ እና ሌሎች ጎረቤት ሃገራት ጋር የነበረውን ግንኙነት መልሶ ያደፈርሰዋል። 
በዚህም ምክንያት በኢትዮጵያ ምናልባትም የዕርስ በዕርስ ጦርነት በድርድርም ሆነ በአሜሪካ ተፅእኖ ሊቆም ቢችልም ሌላ እጅግ የከፋ እና አውዳሚ ጦርነት መቀስቀሱ የማይቀር ነው።
ይሄውም ከኤርትራ ወይንም ከሱዳን እና ግብፅ አሊያም ከሶስቱም ሃገራት ጋር ይሆኖል።
እንግዲህ መንግስት አስተዳደር ላይ ያለው አካል ከህዝብ እና መንግስት ጥቅም አንፃር አይቶ ከአሜሪካ ጋር የመሠረተውን ግንኙነት መፈተሽ ጊዜ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ አይመስለኝም። ካልረፈደ!

በአሁኑ ወቅት ሁለት ዓለማችንን ሊያጠፉ የሚችሉ ስጋቶች (Existential threats)

ስመ ጥሩዉ ይሁዲ አሜሪካዊ የቋንቋ እና የፖለቲካል ፍልስፍና ሊቅ ኖም ቾምስኪ በአሁኑ ወቅት ሁለት ዓለማችንን ሊያጠፉ የሚችሉ ስጋቶች (Existential threats) እውን ወደ መሆን እየተቃረቡ እንደሆነ በተለያዩ ፅሁፎቹ እና በተለያዩ መገናኛ ብዙሃን በሚሰጣቸው ቃለ መጠይቆች ደጋግሞ አሳስቧል። 
ይሄውም አየር(የተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥ እና የኒኩለር ጦርነት ናቸው። 
ቾምስኪ ሁለቱም ዓለማችንን ሊያጠፉ የሚችሉት እነዚህ ስጋቶች ተያያዥ እና መንስዔውም አንድ እንደሆነ ያትታል። 
መንስዔዉም የኒዮሊበራሊዝም ፖለቲካል ኢኮኖሚ ስርዓት መስፋፋት ይሄን ተከትሎ እየሰፈነ የመጣው የኢምፔሪያሊዝም የአስተዳደር ስርዓት እንደሆነ ያስረዳል።
ኒዬሊበራልዚም የፖለቲካል ኢኮኖሚ መሠረቱ "ነፃ ገበያ" መር የንግድ ስርዓት ሲሆን ይሄን ተመክቶ በዓለም ላይ ያለ ሀብትን እና የገንዘብ ተቋምን መቆጣጠር ነው።
እንደ ቾምስኪ ትንታኔ "ነፃ ገበያ" እንደ ስሙ መጀመሪያ "ነፃ" ሳይሆን በብዙ ሸር የታጀበ የመንግስትን እና የህዝብን ሀብት ወደ ግል ንብረትነት ለማዞር ያለመ እና የገንዘብ ተቋማትን ለመቆጣጠር ያለመ የፖለቲካል ኢኮኖሚ ስርዓት ነው። 
ይሄን ለማስፈፀም ደግሞ ሃያላን ሀገራት ባቋቋሙት እንደ የተባበሩት መንግስታት፣ የዓለም ባንክ፣ የዓለም ዓቀፍ የገንዘብ ተቋም፣ የዓለም ንግድ ድርጅት፣ የአውሮፖ ህብረት የመሳሰሉ ግዙፍ ድርጅቶች አጋፋሪነት ከተለያዩ ጠንካራ እና ደካማ ሀገሮች ዘንድ በሚገባ ውል የቁጥጥር መንገዱን ያሰፋል።
ደካማ ሀገራት ከእነዚህ ሃያላን ሃገራት ጋር በሚገቡት ውስብስብ ውል የሀገር ውስጥ ገበያቸውን እና የገንዘብ ተቋማቸውን ለሃያላን ሀገራት ግዙፍ ኩባንያዎች ክፍት እንዲያደርጉ ይገደዳሉ።
ከዚህም አልፎ ሀገራቸውን እና ህዝባቸውን ከችጋር እና ይሄን ተከትሎ ሊመጣ ከሚችል አለመረጋጋት ሊያድን የሚችል የኢኮኖሚ እና የፖለቲካ ፖሊሲ የማውጣት ነፃነታቸውን ያጣሉ። 
ይሄንን አስገዳጅ ዓለም ዓቀፍ ውል ተገን አድርገው የሚመጡ የሃያላን ሃገራት እጅግ ግዙፍ ኩባንያዎችም በቀላሉ ወደ ደካማ ሀገራት ስለሚገቡ እና ስር ስለሚሰዱ የሀገሪቱን ሀብት እና የገንዘብ ተቋም ሀገር ውስጥ ያሉ ጥቃቅን ታዳጊ ኩባንያዎችን በቀላሉ በማሸነፍ እና ከውድድር በማስወጣት ይቆጣጠሩታል።
የአንድን ደካማ ሀገር ሀብት እና የገንዘብ ተቋም ከተቆጣጠርክ ደግሞ የሀገሯን ፖለቲካ በተፈለገው የፖለቲካ ቅርፅ እና ማዕቀፍ ለማደራጀት ምቹ ይሆናል። 
ይሄም ኢምፔሪያሊዝም እንዲሰፍን የሚያደርግ እና የአንድን ሀገር ጥሬ ሀብት የበለጠ ለመበዝበዝ እና ሙሉ የሀገሪቱን ሀብት ለእነዚህ እጅግ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ማዳበሪያነት ለማዋል እንዲጠቀሙበት ያደርጋል። 
ይህ ዞሮ ዞሮ ለበለጠ የአካባቢ ብክለት እና የአየር(ተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥ አደጋ እንዲሁም ድህነት እና ይሄን ተከትሎ ለሚመጣ አለመረጋጋት ስለሚዳርግ ሀገሪቷን እና ህዝቧን የበለጠ ያደቃታል።
በአንድ ሀገር በአየር(የተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥ እና አለመረጋጋት ምክንያት የሚመጣ ድህነት ደግሞ ለበለጠ ቁጥጥር እና የሀብት ምዝበራ ስለሚዳርግ ውጤቱ በመጀመሪያ ደረጃ ችግሩ ወደ ተፈጠረበት ምክንያት ይመራናል።
የበለጠ የሀብት እና የገንዘብ ተቋማት ቁጥጥር እና ኢምፔሪያሊዝም መስፋፋት! 
ይሄን እጅግ የተወሳሰበ መሠሪ የዓለም ስርዓት የሚቃወሙ ሀገራት እና መንግስታትን ደግሞ ከላይ የጠቀስኳቸው ዓለም ዓቀፍ ተቋማት(ድርጅቶች) እርዳታ እና ብድር በመከልከል፣ ማዕቀብ በማድረግ፣ የሀገር ውስጥ ገበያን በማዛባት እና ከዚህም የባሰ ሴራ በመጎንጎን ወደ ተፈለገው የድህነት ቀለበት እንዲገቡ ያስገድዳሉ።
የሀገሩ ህዝብ እና መንግስት ከዚህም የበለጠ ጠንካራ ተቃውሞ እና አቋም የሚያራምድ ከሆነ ደግሞ ሀገሩን እና ህዝቡን የማዳከም ሴራው የበለጠ ግልፅ እየሆነ እና እያየለ ይሄዳል። 
ይሄም ማለት እርስ በእርስ በመከፋፈል እና በማተራመስ፣ የመንግስት ግልበጣ በማድረግ፣ አሊያም የእጅ አዙር ጦርነት በማድረግ እንዲሁም ከዚህም ሲከፋ ቀጥታ ጦር በማዝመት ሀገርህን እና ህዝብህን ሊበትኑት እና መልሶ እንዳይነሳ ሊያደርጉት ይችላሉ። 
ለዚህም ብዙ ርቀህ ሳትሄድ የእኛን ሀገር ኢትዬጵያን፣ ሊቢያን፣ ሶማሊያን፣ ሴሪያን፣ የመንን፣ ኢራቅን፣ ኮንጎን ሌሎች የመካከለኛው ምስራቅ ኤዢያን እና የደቡብ አሜሪካ ሀገራትን ታሪክ መመርመር ከበቂ በላይ ማስረጃ ነው።
ይሄን "በነፃ ገበያ" መር የንግድ ስርዓት መሠረት የሚስፋፋ ኒዬ ሊበራል ፖለቲካል ኢኮኖሚ ፍልስፍናን እና የኢምፔሪያሊዝም አስተዳደር ስርዓትን መስፋፋት በበቂ ሁኔታ የተገዳደሩ እና ሃያላን ምዕራብያዊያን ሀገራትን እየተቋቋሙ የመጡ እንደ ቻይና እና ራሺያ የመሳሰሉ ግዙፍ ሀገራት ከዚህ የድህነት ቀለበት ለመውጣት የሚያደርጉት መፍጨርጨር ደግሞ ሁለተኛውን እጅግ ከባድ ስጋት ደቅኗል። 
ሁለተኛው ከባድ ስጋት ደግሞ መጀመሪያ ላይ እንደገለፅኩት የኒኩለር ጦር መቀስቀስ ስጋት ሲሆን አሁን ሁለቱ የዓለም ክፍሎች የሚገኙበት እጅግ አደገኛ መፋጠጥ ስጋቱን ወደ እውነትነት እያቀረበው ነው።
ራሺያ በዩክሬይን የከፈተችው ጦርነት እንዲሁም ቻይና ከታይዋን ራስ ገዝ አስተዳደር ጋር በተያያዘ የደረሰችበት መካረር እና ከምራብያውያን ጋር ያላቸው መፋጠጥ በማንኛውም ደረጃ ሶስተኛውን የዓለም ጦርነት ሊያስነሳ እና የኒኩለር ጦርነቱን እውን ሊያደርግ የሚችል ነው።
በዚህ መሀል ትልቁ ጥያቄ ሃገርህን እና ህዝብህን እዴት ትታደጋለህ የሚለው ነው?! 
በርግጥ የአየር(የተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥም ሆነ የኒኩለር ጦርነት ዜሮ ድምር ያለው መላ አለምን ሊያጠፋ የሚችል እና አንድ ሀገር እና ህዝብ ከሌላው ተነጥሎ ሊተርፍበት የማይችል ክስተት ቢሆንም እስከዚያው ወደ እዚህ አውዳሚ ጥፋት ሊመራ የሚችል መንገድን ተቋቁሞ መቆየት ማምሻም እድሜ ነው እንደሚባለው ብልህነት ነው።
ለዚህ ግን የህዝብ አንድነት እና ሠላም እጅግ እጅግ ወሳኝ ቁምነገር ሲሆን ይሄንን የሀገር አንድነት እና የህዝብ ሠላም ለማምጣት ግን ከሁሉም ወገን ቅንነት እና ታጋሽነት እንዲሁም ከግል እና የራስ ጥቅም አሻግሮ አስተዋይነት ይጠይቃል። 
በመጀመሪያ ግን ያለውን ስጋት ጠንቅቆ መረዳት እና ማስረዳት ተገቢ እና ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው።
ካልሆነ እያየነው እንዳለው ዓለም በእነዚህ ሁለቱ የአየር(ተፈጥሮ) ፀባይ ለውጥ እና የኒኩለር ጦርነት ምክንያት ካላት የመጥፋት ስጋት ቀድመን እንዳንከስም እሰጋለሁ።